top of page

ዘመን መለወጫ

የኢትዮጵያ የወራት ሁሉ መጀመሪያ መስከረም ነው፡፡ ይህ ወር ዘመን መለወጫ፣ ዕንቁጣጣሽ፣ ቅዱስ ዮሐንስ እየተባለ ይጠራል፡፡ ስለ አዲስ ዓመት በተለያየ ስም የመጠራቱ ታሪካዊ አመጣጥና ስያሜ መነሻ ሃሳቡ ምን እንደሆነ እንደሚከተለው እንመለከታለን፡፡

 

ዘመን መለወጫ

ዘመን መለወጫ መስከረም ወር የሆነበት ምክንያት “ብርሃናት /ፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ከዋክብት/ የዓመት ዑደታቸውን በጳጉሜ ወር ጨርሰው በመስከረም ወር ስለሚጀምሩ ነው፡፡ ሌሊቱ ከቀኑ ጋር ይተካከላል፡፡ ዓመቱን ጠንቅቀው ቢቆጥሩ 364 ቀናት ይሆናል፡፡ “ሌሊቱም ከቀኑ ጋራ ይተካከላል፡፡ ዓመቱም ጠንቅቆ ቢቆጥሩት ሦስት መቶ ስልሳ አራት ቀን ይሆናል፡፡ /ሄኖክ.26፥44/ “ዘመናችንን እንደ ቀድሞ አድሱ” /ሰ.ኤር.5፥21/ እንዲል፡፡

በዘመነ ኖኅ ዓለምን ንፍር ውኃ አጥለቅልቆት ከቆየ በኋላ ዳግመኛ ውኃው የጎደለበት በመሆኑ /ኩፋሌ 7፥1/ “በመጀመሪያው ወር መባቻም ምድር ታየች” እንዲል፡፡

 

ዕንቁጣጣሽ

ዕንቁጣጣሽ የተባለበት ምክንያት አንደኛ “ዕንቁ – ዕፅ አመጣሽ” ብሎ የአበባውን መፈንዳት ያመለክታል፡፡ ሁለተኛ ኖኅ ለሦስቱ ልጆቹ አህጉራትን በእጣ ሲያካፍላቸው አፍሪካ ለካም ደረሰችው፡፡ በአፍሪካ ምድርም ሲገባ በመጀመሪያ ያረፈው በኢትዮጵያ ነበር፡፡ ሀገሪቱም በአደይ አበባ አሸብርቃ ነበር፡፡ ወሩ ወርኀ መስከረም በመሆኑ ደስ ብሎት ዕንቁ ዕጣ ወጣሽልኝ በማለት ይህችን ወቅት እንቁጣጣሽ ብሏታል፡፡ ሦስተኛው /1ነገ.10፥1-10/ ኢትዮጵያዊቷ ንግሥት ሣባ /አዜብ የንጉሡን ጥበብ ከመስማት ማየትን መርጣ ወደ ንጉሥ ሰሎሞን ከብዙ ሠራዊቶቿ ጋር የእጅ መንሻ በመያዝ ሄደች፡፡ ንጉሡም በደስታ ተቀብሎ እርሱም “እንቁ ለጣትሽ ጌጥ ይሁንሽ” በማለት አራት አይነት ቀለም የሚታይበት በቀንና በሌሊት የሚያበራ ቀለበት ሰጥቷታል፡፡ ወሩም ወርኀ መስከረም ነበር፡፡ ከዚህ በመነሣት እንቁጣጣሽ የሚለው ስያሜ ወጥቷል፡፡

 

ቅዱስ ዮሐንስ

ሦስተኛው የአዲስ ዘመን ስያሜ ቅዱስ ዮሐንስ ነው፡፡ የመጥምቁ ዮሐንስ ተግባር ለዘመነ ወንጌል በር ወይም መነሻ እንዲሆን ለኢትዮጵያ ዐውደ ዓመት መስከረም አንድ ቀን እንዲከበር አባቶች ወስነዋል፡፡ /ድርሳነ ዮሐንስ አፈወርቅ ገጽ 1-3/. መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ከአዲስ ኪዳን አበው አንዱ የኾነ፣ ንጹሓን ነቢያት፣ ቅዱስ ገብርኤልና አባቱ ዘካርያስ ትንቢት የተናገሩለት፣ ከሕፃንነቱ ጀምሮ ቅኑት እንደ ገበሬ፣ ጽሙድ እንደ በሬ ኾኖ እግዚአብሔርን ያገለገለ፣ በፍጹም ልቡ ዓለምን የናቀ፣ ከተድላዋና ከደስታዋም የተለየ፣ አምላክን ለማጥመቅ የታደለ ሐዋርያ፣ መምህር፣ ሰማዕት፣ ባሕታዊ፣ ነቢይ፣ ጻድቅ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ሰኔ ፴ ቀን የተወለደበት፤ መስከረም ፩ ቀን ቃል ኪዳን የተቀበለበት፤ መስከረም ፪ ቀን በሰማዕትነት ያረፈበት፤ ጥር ፲፩ ቀን ጌታችንን ያጠመቀበት፤ የካቲት ፴ ቀን ራሱ የተገኘችበት፤ ሚያዝያ ፲፭ ቀን ራሱ ያረፈችበት (ነፍሱ የወጣችበት)፤ ሰኔ ፪ ቀን ደግሞ ፍልሰተ ዐፅሙ (ዐፅሙ የፈለሰበት) በዓል በቤተ ክርስቲያናችን ይከበራል፡፡

 

በአጠቃላይ ዘመን መለወጫ ከላይ ባየናቸው የተለያየ ስያሜ ይጠራ እንጂ ዘመኑ አዲስ እየተባለ ቢጠራም አዲስ መሆን ያለበት ወርና ወቅቱ ብቻ ሳይሆን የእኛ የክርስቲያኖች ሥርዓት ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰውነታችሁን አታርክሱ የእግዚአብሔር ማደሪያ ነውና እያለ በመዋዕለ ሥጋዌው ያስተምር ነበር፡፡ አዲስ ዓመት ሲመጣ በኀጥያት፣ በተንኮል፣ በክፋት የቆሸሸው ሰውነታችን በንስሓ፣ በቅዱስ ቊርባን፣ በመልካም ተግባር አዲስ ልናደርገው ይገባናል፡፡ 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፣ማህበረ ቅዱሳን መካነ ድር

የመስቀል በዓል

የመስቀል በዓል የሚከበረው መስከረም 17 ቀን ነው። የሚከበርበትም ምክንያት፡- ጌታ በመስቀል ላይ ሙቶ ከተነሣ በኋላ ሕሙማን መስቀሉን እየዳሰሱ በመስቀሉ እየታሹ ይፈውሱ ነበር። ይህንን ያዩ አይሁድም በምቀኝነት መስቀሉን ከቆሻሻ ማጠራቀሚያ ቦታ ጣሉት። ከብዙ ጊዜም በኋላ ያ ቦታ እንደ ጉብታ ሆነ። ምንም እንኳ ለማውጣት ባይችሉ ክርስቲያኖቹ ያን ቦታ ያውቁት ነበር። በኋላ ግን በ70 ዓ.ም. በጥጦስ ወረራ ክርስቲያኖቹ ኢየሩሳሌምን ለቀው ስለወጡና የከተማዋም መልክ ስለተለወጠ መስቀሉ የተቀበረበትን ጉብታ ለማወቅ አልተቻለም። በዚህም ምክንያት ለሦስት መቶ ዓመታት ያህል ተዳፍኖ ቆይቷል። በኋላ ላይ ግን በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የታላቁ ንጉሥ የቆስጠንጢኖስ እናት ንግሥት እሌኒ ወደ ኢየሩሳሌም ሄዳ መስቀሉን ለማውጣት ብዙ ደከመች። በመጨረሻም ስሙ ኪርያኮስ የተባለ አረጋዊ በነገራት መሠረት ደመራ አስደምራ ዕጣን አፍስሳበት በእሳት ብትለኩሰው ጢሱ እንደ ቀስተ ደመና መስቀሉ ከተቀበረበት ጉብታ ላይ ተተክሎ በጣት ጠቅሶ የማሳየት ያህል አመልክቷታል። ሳትውል ሳታድር መስከረም 17 ቁፋሮ አስጀምራ መጋቢት 10 መስቀሉን አግኝታለች። ቅዳሴ ቤት /ቤተመቅደስ/ ተሠርቶ የተፈጸመው በመስከረም 17 ነው።  እንደወጣም ብዙ ተዓምራትን አድርጓል።
 
    እንግዲህ በሀገራችን በኢትዮጵያ የመስቀልን በዓል ደመራ በመደመርና ችቦ በማብራት፥ ቅዳሴ በመቀደስና ማኅሌት በመቆም የምናከብረው ለዚህ ነው። በዚሁም ላይ ይህን ታላቅ ዕፀ መስቀል በወቅቱ የነበሩ ታላላቅ ነገሥታት የሚያደርጋቸውን ተዓምራት በማየት ለእያንዳንዳቸው ይደርሳቸው ዘንድ ከአራት ክፍል ሲከፍሉት ከአራቱ አንዱ የቀኝ እጁ ያረፈበት ግማድ /ክፋይ/ ብቻ በደብረ ከርቤ ግሸን ማርያም ሲገኝ ሌሎች ሦስቱ ግን የት እንደደረሱ አይታወቅም። ይህም ግማደ መስቀል የመጣው በአፄ ዳዊት በ14ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ሲሆን ኢትዮጵያ ከገባ በኋላ የማስቀመጫ መቅደስ ለማሠራት መሬቱ እየተንቀጠቀጠ አልረጋ ብሏቸው በርካታ አድባራትን ካዳረሱ በኋላም እግዚአብሔር “አንብር መስቀልየ በዲበ መስቀል /መስቀሌን በመስቀለኛ ቦታ አስቀምጥ/” ብሎ ስለነገራቸው ተፈልጋ ግሸን ደብረ ከርቤ በተባለው ቦታ የመስቀል ቅርጽ ስለተገኘች ዛሬም ድረስ በዚሁ ታላቅ ቦታ ይገኛል። በዚህ ታላቅ ጸጋ የተጠቀሙት ብዙዎች ናቸውና እኛንም ከዚህ ረድኤት እንዲከፍለን በዓሉን በአግባቡና በሥርዓት ልናከብረው ያስፈልጋል። መልካም በዓል አክብረን የመስቀሉ ክብርና ጸጋ ረድኤት ይድረሰን። አሜን።

ምንጭ፣ማኅበረ ቅዱሳን አሜሪካ ማዕከል 

ዘመነ ጽጌ

በቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ፣ በአገራችን በኢትዮጵያ የወቅቶች ሥርዓተ ዑደት መሠረት ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፮ ቀን ድረስ ያሉትን ፵ ቀናት ያካተተው ወቅት ዘመነ ጽጌ ተብሎ ይጠራል፡፡ ‹ጽጌ› ቃሉ ‹ጸገየ አበበ› ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲኾን ትርጕሙም አባባ ማለት ነው፡፡ ‹ዘመነ ጽጌ› ደግሞ ‹የአበባ ወቅት፣ የአበባ ጊዜ፣ የአበባ ዘመን› ማለት ነው፡፡ ይህ ወቅት ዕፀዋት በአበባ የሚያጌጡበት፣ ምድር በአበቦች ኅብረ ቀለማት የምታሸበርቅበት፣ ወንዞች ንጹሕ የሚኾኑበት፣ ጥሩ አየር የሚነፍስበት፣ አዕዋፍ በዝማሬ የሚደሰቱበት፣ እኛም የሰው ልጆች ‹‹አሠርጎካ ለምድር በሥነ ጽጌያት፤ አቤቱ ምድርን በአበቦች ውበት አስጌጥሃት›› እያልን የዘመናት አስገኚና ባለቤት የኾነውን ልዑል እግዚአብሔርን የምናመሰግንበት፤ ከዚህም ባሻገር እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከተወደደ ልጇ ከጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ከገሊላ ወደ ግብጽ ምድር መሰደዷን የምናስብበት ወቅት ነው፡፡ 

 

ይኽን የመከራ እና የስደት ወቅት በማሰብ ረኃብ ጥሙን ፤የቀን ሐሩሩን የሌት ቁሩን ፤ከልጅሽ ጋር የተቀበልሽውን መከራ አሳስቢ እያሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ካህናትና ምእመናን በረከት እናገኝበታለን ብለው  የሚጾሙት የፈቃድ ጾም የጽጌ ጾም እየተባለ ይጠራል፡፡ 

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቤተልሔም በተወለደ ጊዜ የዘመኑ ንጉሥ ሄሮድስ ሥልጣኔን ይቀማኛል በሚል ቅናት ተነሣሥቶ ጌታችንን ለማስገደል አሰበ፡፡ ያንጊዜም ጌታችን በተአምራት መዳን ሲቻለው የትዕግሥት፣ የትሕትና አምላክ ነውና በለበሰው ሥጋ በእናቱ በቅድስት ድንግል ማርያም ጀርባ ታዝሎ በመልአኩ ተራዳኢነት፣ በአረጋዊው ዮሴፍ ጠባቂነትና በሰሎሜ ድጋፍ ከገሊላ ወደ ግብጽ ተሰዶ ሄሮድስ እስኪሞት ድረስ ቆይቷል፡፡ ሄሮድስም ጌታን ያገኘ መስሎት በቤተ ልሔምና በአውራጃዋ የሚገኙ ሁለት ዓመት እና ከዚያ በታች የኾኑ አንድ መቶ ዐርባ አራት ሺሕ ሕፃናትን በግፍ አስፈጅቷል፡፡

በተአምረ ማርያምና በማኅሌተ ጽጌ ተጽፎ እንደሚገኘው ጌታችን በግብጽ ምድር በስደት ሳለ ብዙ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን አድርጓል፡፡ ከእነዚህ መካከልም እናቱን እመቤታችንን የዘለፏትን ትዕማንና ኮቲባ የሚባሉ ሴቶችን ከሰውነት ወደ ውሻነት መቀየሩ፤ ውሃ በጠማቸው ጊዜ ውሃ እያፈለቀ ማጠጣቱና ይህንን ውሃ ክፉዎች እንዳይጠጡት መራራ ማድረጉ፤ ለችግረኞችና ለበሽተኞች ግን ጣፋጭ መጠጥና ፈዋሽ ጠበል ማድረጉ፤ ‹‹የሄሮድስ ጭፍሮች ደርሰው ልጅሽን ሊገድሉብሽ ነው›› ብሎ የዮሴፍ ልጅ ዮሳ እመቤታችንን በማስደንገጡ እስከ ዕለተ ምጽአት ድረስ ድንጋይ ኾኖ እንዲቆይ ማድረጉ፤ መንገድ ላይ የተራዳቸው ሽፍታ ሰይፉ በተሰበረች ጊዜ እንደ ቀድሞው ደኅና እንድትኾን ማድረጉ፤ እንደዚሁም የግብጽ ጣዖታትን ቀጥቅጦ ማጥፋቱ ተጠቃሾች ናቸው፡፡

የጌታችንና የእመቤታችን የስደት ወቅት በወርኀ ግንቦት ነው፤ ነገር ግን ዘመነ ጽጌ የአበባና የፍሬ ወቅት በመኾኑ እመቤታችንን በአበባ፣ ጌታችንን ደግሞ በፍሬ እየመሰሉ ለማመስገንና ለማወደስ በሚያስችል ምሥጢር ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የስደቱ ጊዜ በዘመነ ጽጌ እንዲዘከር አድርገዋል፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለዘለዓለሙ የማይደርቀውን የሕይወት ፍሬ ኢየሱስ ክርስቶስን ያስገኘችልን ንጽሕት የማትጠወልግ አበባ ናትና፡፡ ይህ የእመቤታችን አበባነትና የጌታችን ፍሬነትም እንደ ቅዱስ ያሬድ፣ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫና አባ ጽጌ ድንግል ባሉ ሊቃውንት ድርሰቶች በሰፊው ተገልጧል፡፡

በዘመነ ጽጌ በማኅሌትና በቅዳሴ ጊዜ የሚቀርቡ መዝሙራትና የሚሰጡ ትምህርቶችም ይህንኑ ምሥጢር የሚመለከቱ ናቸው፡፡ በዚህ ወቅት በሚገኙ ሰንበታትም ሊቃውንቱ ሌሊቱን ሙሉ ስለ እመቤታችን አበባነትና ስለ ጌታችን ፍሬነት የሚያትት ትምህርት የያዙትን ማኅሌተ ጽጌና፣ ሰቆቃወ ድንግልን ከቅዱስ ያሬድ ዚቅ ጋር በማስማማት ሲዘምሩ፣ ሲያሸበሽቡ ያድራሉ፡፡ ቅዳሴውም በአባ ሕርያቆስ የተደረሰውና ምሥጢረ ሥጋዌን፣ ምሥጢረ ሥላሴንና ነገረ ማርያምን የሚተነትነው ቅዳሴ ማርያም ነው፡፡ ምንባባቱም ከዚሁ ጋር ተዛማጅነት ያላቸው ናቸው፡፡

በአጠቃላይ እመቤታችን በስደቷ የደረሰባትን መከራ በማስታዎስ ዘመነ ጽጌን በፈቃዳቸው የሚጾሙ ካህናትና ምእመናን ብዙዎች ናቸው፡፡ ኾኖም ግን የጽጌ ጾም የፈቃድ ጾም እንጂ ከሰባቱ አጽዋማት ጋር የሚመደብ ስላልኾነ ጽጌን የማይጾሙ አባቶች ካህናትንና ምእመናንን ልንነቅፋቸው አይገባም፡፡ አምላካችን በአበባ የሚመሰለው ሰውነታችን የጽድቅ ፍሬን ሳያፈራ በሞት እንዳንወሰድ መልካም ፈቃዱ ይኹንልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር።

ምንጭ፣ማህበረ ቅዱሳን መካነ ድር

 የቀዳሚ ሰማዕት ሊቀ ዲያቆናት ቅዱስ እስጢፋኖስ የሹመት ቀን

ቤተክርስቲያናችን በየአመቱ ጥቅምት ፲፯ የቀዳሚ ሰማዕት የሊቀ ዲያቆናት ቅዱስ እስጢፋኖስ የተሾመበትን ቀን ታከብራለች፤መስከረም ፩፭ ፍልሰተ አጽሙ ነው ጥር ፩ እረፍቱ ነው፤ እነዚህ ፫ ቀናት ሰማዕቱ በሰፊው ይዘከርባቸዋል።

 

ቅዱስ እስጢፋኖስ አባቱ ስምኦን እናቱ ማርያም ስና ይባላሉ፤የአብርሃም ዘር አይሁዳዊ ናቸው ልጃቸውን በጥበብ አሳደጉት፤ እስጢፋኖስ ማለት ወደብ ጸጥታ ማለት ነው። ምነዋ ቀዳሚ ሰማዕት ተባለ ቀደምት ነብያት በመጋዝ ተሰንጥቀው እንደ ሽንኩርትም ተቀርድደው የለም ወይ ቢሉ ከጌታችን እርገት በኃላ የመጀመሪያው ሰማዕት እርሱ ስለሆነ ነው፤ ሊቀ ዲያቆናት ያሰኘው ቅሉ በሐዋርያት ስራ ፮፤፭ ከተመረጡት ፯ ዲያቆናት አለቃቸው ስለሆነ ነው።

 

አይሁድ አማጽያን ሊሞግቱት በሸንጎ ተሰበሰቡ መጽሐፍ እንደመሰከረው እስጢፋኖስም ጸጋንና ኃይልን ተሞልቶ በሕዝቡ መካከል ድንቅንና ታላቅ ምልክትን ያደርግ ነበር፤ ይናገርበት የነበረውንም ጥበብና መንፈስ ይቃወሙ ዘንድ አልቻሉም ይላል፤ “አንገተ ደንዳኖች ልባችሁና ጆሮአችሁም ያልተገረዘ” ብሎ በግልጽ ዘለፋቸው ስለ ጌታችን መሰከረ በዚህም ተቆጡ ድንጋይ ጨበጡ በግፍ ገደሉት ይቅር በላቸው እያለ ነፍሱን ሰጠ፤ ጥቅምት ፲፯ ይህን ቀን የሰማዕቱ ታቦት በሚገኝበት ሁሉ በደማቁ ተከብሮ ይውላል፤ ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን።

ጾመ ነቢያት

ጾመ ነቢያት በየዓመቱ ከኅዳር ፲፭ ቀን ጀምሮ እስከ በዓለ ልደት ዋዜማ ድረስ የሚጾም፤ ከሰባቱ አጽዋማት መካከል አንደኛው ጾም ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ዓለምን ለማዳን ሲል የሰውን ሥጋ ስለ መልበሱ፤ ወደ ግብጽ ስለ መሰደዱ፤ በባሕረ ዮርዳኖስ ስለ መጠመቁ፤ በትምህርቱ ብርሃንነት ጨለማውን ዓለም ስለ ማብራቱ፤ ለሰው ልጆች ድኅነት ልዩ ልዩ መከራን ስለ መቀበሉ፤ ስለ መሰቀሉ፣ ስለ ሞቱ፣ ትንሣኤው፣ ዕርገቱና ዳግም ምጽአቱ በየዘመናቱ የተነሡ ቅዱሳን ነቢያት በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝተው ትንቢት ተናግረዋል፤ ትንቢቱ ደርሶ፣ ተፈጽሞ ለመመልከትም ‹‹አንሥእ ኃይለከ ፈኑ እዴከ፤ ኃይልህን አንሣ፤ እጅህን ላክ›› እያሉ በጾም በጸሎት ተወስነው አምላክ ሰው የሚኾንበትን ጊዜ በቀናት፣ በሳምንታት፣ በወራትና በዓመታት እያሰሉ ሲጠባበቁ ቆይተዋል፡፡

ይህ ጾም የእግዚአብሔርን ሰው መኾን ሲጠባበቁ የኖሩት የነቢያት ትንቢትና ጸሎት በጌታችን መወለድ ፍጻሜ ያገኘበት ወቅት በመኾኑ ‹‹ጾመ ነቢያት (የነቢያት ጾም)›› እየተባለ ይጠራል፡፡ ለአዳም የተነገረው የድኅነት ተስፋ ስለተፈጸመበትም ‹‹ጾመ አዳም (የአዳም ጾም)›› ይባላል፡፡ ስለ እግዚአብሔር ሰው መኾን በስፋት ትምህርተ ወንጌል የሚሰጥበት ወቅት በመኾኑም ‹‹ጾመ ስብከት (የስብከት ጾም)››፤ የጾሙ መጨረሻ (መፍቻ) በዓለ ልደት በመኾኑ ደግሞ ‹‹ጾመ ልደት (የልደት ጾም)›› በመባል ይታወቃል፡፡ እንደዚሁም ‹‹ጾመ ሐዋርያት›› ይባላል፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት ‹‹በዓለ ትንሣኤን ዐቢይ ጾምን ጾመን እናከብረዋለን፤ በዓለ ልደትንስ ምን አድርገን እናከብረዋለን?›› በማለት ነቢያት የጾሙትን ከልደተ ክርሰቶስ በፊት ያለውን ጾም ጾመዋልና፡፡

በተመሳሳይ መልኩ ይህ ጾም ‹‹ጾመ ፊልጶስ (የፊልጶስ ጾም)›› ተብሎ ይጠራል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ፊልጶስ በአፍራቅያና አውራጃዋ ዅሉ እየተዘዋወረ በጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ወንጌልን በማስተማር፣ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን በማድረግ ብዙዎችን ወደ አሚነ እግዚአብሔር ሲመልስ ቆይቶ ትምህርቱን በማይቀበሉ የአፍራቅያ ሰዎች አማካይነት በሰማዕትነት ዐርፏል፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ሥጋውን ሊቀብሩ ሲሉም ስለ ተሰወረባቸው የሐዋርያውን ሥጋ ይመልስላቸው ዘንድ ሱባዔ ይዘው፣ በጾም በጸሎት ተወስነው በለመኑት ጊዜ እግዚአብሔር ልመናቸውን ተቀብሎ በ፫ኛው ቀን መልሶላቸው ሥጋውን (አስከሬኑን) በክብር አሳርፈውታል፡፡ ደቀ መዛሙርቱ የሐዋርያውን ሥጋ ካገኙ በኋላ እስከ ጌታችን ልደት ድረስ ጾመዋል፡፡ ስለዚህም ጾመ ነቢያት ‹‹ጾመ ፊልጶስ›› እየተባለ ይጠራል፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም ወልደ አምላክ ክርስቶስን በግብረ መንፈስ ቅዱስ እንደምትፀንሰው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ካበሠራት በኋላ እመቤታችን ‹‹ሰማይና ምድር የማይወስኑትን አምላክ ፀንሼ ምን ሠርቼ እወልደዋለሁ?›› በማለት ጌታችንን ከመውለዷ አስቀድማ ጾማዋለችና ይህ ጾም ‹‹ጾመ ማርያም›› በመባልም ይታወቃል፡፡

በአጠቃላይ በዚህ በገና ጾም ነቢያትም ሐዋርያትም ጾመው በረከት አግኝተውበታል፡፡ እኛ ምእመናንም እንደ እነርሱ በረከትን እናገኝ ዘንድ ይህንን ጾም መጾም እንደሚገባን የቤተ ክርስቲያን አባቶች ሥርዐት ሠርተውልናል፡፡ በዚህም መሠረት የነቢያት፣ የሐዋርያት፣ የጻድቃንና የሰማዕታት አምላክ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ከቅዱሳን ነቢያትና ሐዋርያት በረከት እንዲያሳትፈን፤ መንግሥቱንም እንዲያወርሰን ዅላችንም በዚህ በጾመ ነቢያት ወቅት በጾም በጸሎት ተወስነን እግዚአብሔርን ልንማጸነው ይገባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡-

ፍትሐ ነገሥት ንባቡና ትርጓሜው፣ አንቀጽ ፲፭፡፡

ጾምና ምጽዋት፣ ዲያቆን ቃኘው ወልዴ፤ ገጽ ፵፯ -፶፡፡

 

ልደተ ክርስቶስ /የገና በዓል/

ይህ ዕለት የጌታችን፤ የአምላካችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ልደት የምናስብበት ቀን ነው። ዓመተ ፍዳና ዓመተ ኵነኔ በመባል የሚታወቀው የጥፋት ዘመን የተሻረበትና በነቢዩ በኢሳያስ ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና፤ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፤ ስሙም ድንቅ መካር፥ ኃያል አምላክ፥ የዘላለም አባት፥ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል። ኢሣ.፱፡፮ ተብሎ የተነገረው የትንቢት ቃል ፍጻሜን አግኝቶ ኢየሱስ ክርስቶስ የተወለደበት ይኽ ቀን የባርነት ሰንሰለት የተፈታበትና ዓመተ ምሕረት ተብሎ የተነገረበትም ታላቅ ወቅት ነው።

 

በጨለማ የሚኖር ሕዝብ ብርሃንን ያየበት ይኽ ቀን ልዩና ድንቅ በመሆኑ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፦  እግዚአብሔርንም የመምሰል ምሥጢር ያለ ጥርጥር ታላቅ ነው፤ በሥጋ የተገለጠ፥ በመንፈስ የጸደቀ፥ ለመላእክት የታየ፥ በአሕዛብ የተሰበከ፥ በዓለም የታመነ፥ በክብር ያረገ። በማለት ይኸን ታላቅ ምሥጢር በታላቅ መገረም በጢሞቴዎስ መልእክቱ ምዕራፍ ፫፡፲፮ ላይ አስፍሮታል። የማይወሰነው ተወስኖና በታላቅ ትሕትና የባሪያን መልክ ይዞ ወደ ምድር የመጣው ኢየሱስ ክርስቶስ የዲያብሎስን ሥራ ሊያፈርስና የጠፋውን ሊፈልግ ነው።

ኢየሱስ ክርስቶስ ሲወለድ የነበሩ ሁኔታዎች፦ ሰብዓ ሰገል ኮከቡን በምሥራቅ አይተው ወደ ኢየሩሳሌም መምጣታቸውን ንጉሡ ሄሮድስ በሰማ ጊዜ እንደ ጀምበር ለሚጠልቅና ታይቶ ለሚጠፋ ሥልጣን ተጨንቆ ዓለምን ለማዳን የመጣውን ጌታ የምድር ሥልጣኑን ሊወስድበት እንደሆነ በመገመት ከካህናት አለቆች ከጻፎች ስለ ሁኔታው ለማወቅ ጌታ የት እንደሚወለድ ይጠይቅ ጀመር። እነርሱም በነቢያት የተጻፈውን ትንቢት እንዲህ እንደሚል ነገሩት፦ አንቺም ቤተልሔም ኤፍራታ ሆይ፥ አንቺ በይሁዳ አእላፋት መካከል ትሆኚ ዘንድ ታናሽ ነሽ፤ ከአንቺ ግን አወጣጡ ከቀድሞ ጀምሮ ከዘላለም የሆነ፥ በእስራኤልም ላይ ገዥ የሚሆን ይወጣልኛል። ሚክ. ፭፡፪ ሄሮድስ ይኸን ቃል ሲሰማ እጅግ በመደናገጡና የኢየሱስ ክርስቶስም መወለድ ለሥልጣኑ እንደሚያሳስበው በመገመት ሰብዓ ሰገልን በስውር ጠርቶ ሕፃኑን ባገኛችሁት ጊዜ እኔ ደግሞ መጥቼ እንድሰግድለት ንገሩኝ በማለት በሐሰት የተቀመመና በሬት የተለወሰ እውነት የሚመስል ከንቱ አነጋገርን ተናገራቸው።

 

ሰብዓ ሰገል ጌታ በኢየሩሳሌም እንደሚወለድ እንጂ በየት ሥፍራ እንደሚወለድ አያውቁም ነበር። ሆኖም ግን በምሥራቅ ያዩት ኮከብ እየመራ ጌታችን እስከተወለደበት ስፍራ ድረስ አድርሷቸው ቆመ። ዓለም ዛሬ በደረሰበት ሥልጣኔ ከቦታ ወደ ቦታ ለመዘዋወር ጂፒኤስ በሚባል መሣሪያ ሲንቀሳቀስና ወዳሰበበት ቦታ ያለ ችግር መድረሱ ገሐድ የሆነለት በቅርብ ጊዜ ሲሆን ሰብዓ ሰገል ግን በእግዚአብሔር ፍቃድ ከሁለት ሺህ ዓመታት በፊት ኮከብ እየመራቸው ጌታ የተወለደበት ስፍራ አድርሷቸዋል። ከሁሉ የሚገርመው ደግሞ ሰብዓ ሰገል የሄሮድስን ትእዛዝ ሰምተው ወደ ኢየሩሳሌም እንዳይመለሱ ሦስቱም አንድ ዓይነት ኅልም ማየታቸው ነው። በኮከብ እየተመሩ ጌታ ከተወለደበት የደረሱት የጥበብ ሰዎች በሕልም ተነግሯቸው ደግሞ በሌላ አቅጣጫ ወደ መጡበት ስፍራ ተመልሰዋል።

 

ለሰብዓ ሰገል በኅልም አቅጣጫን ያመላከታቸው እግዚአብሔር ለዮሴፍም የጌታ መልአክ በኅልም ታይቶ እንዲህ ሲል መልእክትን ነገረው፦  ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይፈልገዋልና ተነሣ፥ ሕፃኑንና እናቱንም ይዘህ ወደ ግብፅ ሽሽ፥ እስክነግርህም ድረስ በዚያ ተቀመጥ አለው። እርሱም ተነሥቶ ሕፃኑንና እናቱን በሌሊት ያዘና ከጌታ ዘንድ በነቢይ። ልጄን ከግብፅ ጠራሁት የተባለው እንዲፈጸም ወደ ግብፅ ሄደ፥ ሄሮድስም እስኪሞት ድረስ በዚያ ኖረ። ማቴ.፪፡፲፫-፲፭

 

ስለ ምድራዊ ሥልጣን የሄሮድስ ጭካኔ፦ ሰብዓ ሰገል ወደ እርሱ አለመምጣታቸውን ሄሮድስ ሲረዳ በቤተልሔም አውራጃ የሚገኙትን ሕፃናት አስገደላቸው። በዚህም አስቀድሞ በነቢያት ተነግሮ የነበረው ትንቢት በጨካኙ ሄሮድስ ተፈጸመ፦  የዋይታና የመራራ ልቅሶ ድምፅ በራማ ተሰማ፤ ራሔል ስለ ልጆችዋ አለቀሰች፤ የሉምና ስለ ልጆችዋ መጽናናትን እንቢ አለች። ኤር. ፴፩፡፲፭ የእናት ጡት ያልጠገቡ፣ ንግግር የማያውቁትንና ገና በእናታቸው እቅፍ ያሉትን ሕፃናትን ሄሮድስ በግፍ አስጨረሳቸው። እንደ እግዚአብሔር መሆን ፈልጎ ያልተሳካለት እና ያለግብሩ አምላክነትን የከጀለው ሰይጣን ዲያብሎስ ከክብሩ እንደተዋረደ ባወቀ ጊዜ አዳምንና ሔዋንን አሳስቶ ከገነት እንዳስወጣቸው ሁሉ አሁንም በሄሮድስ ላይ አድሮ ሕፃናቱን በሙሉ አስጨረሰ። ሄሮድስ ከዓመተ ፍዳ እንዲወጣና ነፃነትን ገንዘብ እንዲያደርግ ወደ ምድር የመጣውን ኢየሱስ ክርስቶስን የምድር ሥልጣን ተጋሪው አድርጎት ለከንቱ ሥልጣን ሕፃናቱን እንዳስጨረሰ ሁሉ ዛሬም ምድራችን ለከንቱ ዝና ብቻ በመቆም በቤተ ክርስቲያን ሰላም እንዳይመጣ በማስደረግ ሕፃናት ነገ የእውነተኛይቱ ሃይማኖት ተረካቢ እንዳይሆኑ የሚያደርጉ ብዙ ሰዎችን አፍርታላች። የሄሮድስን ጭካኔ ገንዘብ ከማድረግ ይልቅ በክርስቶስ ያገኘነውን ሰላም ተጠቅመን ሕዝባችንን ከችግር ለማውጣት የየበኩላችንን ጥረት ማድረግ ይጠበቅብናል።

 

የጌታችን ልደት የእኩልነት ቀን ነው፦ ጌታችን ሲወለድ ሀብት ያላቸው ሰብዓ ሰገል፣ በድህነት ያሉ እረኞች፣ በሰማይ ያሉ መላእክት፣ በምድር ያሉ እንስሳት ተገኝተዋል። ዛሬም የጌታችንን መወለድ ሰምተው የሚደሰቱ እልፍ አዕላፍ ሰዎች በምድር ላይ አሉ። በአንፃሩም እንደ ሄሮድስ ዓይነቶች ከክብር ይልቅ ውርደትን፣ ከሰላም ይልቅ ሁከትን፣ ከማመን ይልቅ አለማመንን የመረጡ ብዙዎች አሉ። የተወለደው የሰላም አምላክ ሁላችንን የሚጠብቅ እረኛችን ነውና ከዚህ በረት ያልሆኑ ነገር ግን ወደዚህ በረት መግባት የሚገባቸው ብዙ በጎች አሉኝ ብሎ እንደተናገረው የአምላካችንን ፍቅር ቀምሰው ይረኩ ዘንድ እግዚአብሔር በተለየ ጥበቡ ወደ በረቱ ይመልሳቸው። የጌታችን መወለድ የእኩልነት ቀን መሆኑን ካመንን እኛ ፍጥረቶቹ ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ብለው ሰውና መላእክት እንዳመሰገኑት ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ በማለት ልናመሰግነው ይገባናል። አምላክ ሰው ሰው አምላክ የሆነበት ይኽ ታላቅ ቀን ተዋሕዶነትን መሥርቶልናል። በልደቱ ሰላምን፣ አንድነትን፣ ክብርን፣ ፍቅርን፣ ትሕትናን፣ ውሕደትን ገንዘብ አድርገናል።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፦ በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ/ሰ/አ/ሰ/ት/ቤቶች አንድነት ጉባኤ

ቅድስት ሥላሴ

በዚህች ቀን ቅድስት ሥላሴ በኃጢያት የተገነባውን የሰናኦር ግንብ ያፈረሱበት አንድነታቸውንና ሶስትነታቸውን በግልጽ ያሳዩበት ቀን ነው፤ ሙሉ ታሪኩ ዘፍጥረት 11 ፤1 ላይ ይገኛል፤ "እግዚአብሔርም የአዳም ልጆች የሠሩትን ከተማና ግንብ ለማየት ወረደ። እግዚአብሔርም አለ። ኑ፥ እንውረድ፤ አንዱ የአንዱን ነገር እንዳይሰማው ቋንቋቸውን በዚያ እንደባልቀው። እግዚአብሔርም ከዚያ በምድር ሁሉ ላይ በተናቸው፤ ከተማይቱንም መሥራት ተዉ። ስለዚህም ስምዋ ባቢሎን ተባለ" ይላል።

 

( “እግዝያብሔርም አለ” አንድነታቸውን ሲያጠይቅ ኑ እንውረድ ሶስትነታቸውን፤) ሥላሴ በስም አአካል በግብር ሶስት ናቸው፤የስም ሶስትነታቸው እንደምን ነው ቢሉ አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ማለት ነው፤ የግብር ሶስትነታቸውስ እንደምን ነው ቢሉ አብ ወላዲ ወልድ ተወላዲ መንፈስ ቅዱስ ሰራጺ፤የአካል ሶስትነታቸውስ እንዴት ነው ቢሉ ለአብ ፍጹም አካል ፍጹም ገጽ ፍጹም መልክ አለው ለወልድም ፍጹም አካል ፍጹም ገጽ ፍጹም መልክ አለው ለመንፈስ ቅዱስም ፍጹም አካል ፍጹም ገጽ ፍጹም መልክ አለው፤ ለመሆኑ የሥላሴ ገጽ አካል ፊት እንደ ሰው ነውን ቢሉ አዎን እንደ ሰው ነው ነገር ግን የሰው ውሱን ጠባብ ፈራሽና በስባሽ ነው የሥላሴ ግን እንዲህ አይደለም በሰማይና በምድር በአየርና በእመቅ የመላ ረቂቅ ህያው ባህርይ ነው ኢሳ 66 ፤ 1። የሥላሴ አንድነታቸው በመለኮት በፈቃድ በስልጣን በምክር ወዘተ በመሳሰሉት ነው።

ገሃድ/ ጾመ ድራረ ጥምቀት

ይህ ጾም የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ጥምቀት በማሰብ የጥምቀትን ዋዜማ መጾም ነው፡፡ ይህም ማለት በጥምቀት ዋዜማ ከምግብ መከልከል ነው፡፡ የሚቆርብ ሰው አክፍሎ የሚያድር ስለሆነም የጥምቀትን ድራር መጾም ነው፡፡ ሐዋርያት «ልደት ጥምቀት ዓርብ ረቡዕ ቢውል በሌሊት ቀድሰው ሥጋውን ደሙን ይቀበሉ፤ ከሌሊቱ እስከ ዘጠኝ ሰዓት ጹሙ ብለው አይፍረዱ» ብለዋል /ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 15/፡፡ የልደትና የጥምቀት በዓል በረቡዕ ወይም በዓርብ ቀን ቢሆን በበዓለ ሃምሳ የሚበላውን የጥሉላት ምግብ በጠዋት በመብላት ምእመናን በዓሉን እንዲያከብሩ ታዟል፡፡

ይህም እነዚህ ሁለቱ ታላላቅ የእግዚአብሔር በዓላት በመሆናቸው ነው፡፡ የጥምቀት በዓል በረቡዕና በዓርብ በሚውልበት ጊዜ በረቡዕና በዓርብ ፈንታ ማክሰኞንና ሐሙስን በመጾማችን ሁለት ሥራ ይፈጸምልናል፡፡ በዚህም የጾምና የበዓል ማክበር ሥራ ይከናወናል፡፡ የጥምቀትን ዋዜማ ጥሉላት መባልዕትን መተው ነው፡፡ ይህንንም እንደ ዘይቤው ገሀድ ይለዋል፣ መገለጫ፣ ግልጥ፣ ይፋ መሆን ማለት ነው፡፡ እንዲሁም ጋድ ይለዋል፣ ለውጥ፣ ልዋጭ ማለት ነው፡፡ ጥምቀት ረቡዕ ዓርብ ሲውል በዚያ ለውጥ ማክሰኞ ሐሙስ ይጾማልና ጋድ አለው፡፡ እንዲሁም አንድ ጊዜ ሲጾም አንድ ጊዜ ሲቀር እንዳይረሳና ቅዳሜ ወይም እሑድ በሰንበት ቀን ይጾሙ ዘንድ አይቻልም፣ ነገር ግን እህል ውኃ እንጂ ጥሉላት ከመብላት መጠበቅ ይገባል፡፡

ልደት የሚውልባቸው ረቡዕና ዓርብ ቢሆኑ የፍሥክ /የሚበላባቸው/ ቀናት ሆነው እንዲከበሩ ሐዋርያት ያዘዙ ቢሆንም በዋዜማው የሚገኙት ማክሰኞና ሐሙስ ከጾመ ነቢያት ጋር የተያያዙ ስለሆኑ መጾማቸው ግድ ነው፡፡ ሆኖም የነቢያትን ጾም የማይጾሙ ሰዎች በመላው የጾሙ ቀናት ሲበሉ ቆይተው በዋዜማው ብቻ ገሀድ ነው ብለው ይጾማሉ፡፡ ነገር ግን ለጾመ ነቢያት ገሀድ የለውም፡፡ ጾሙ የጥምቀት ብቻ መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ለጾመ ነቢያት ገሀድ እንዳለው የሚናገሩም አሉ፡፡ ለዚህም የሚያቀርቡት ማስረጃ እስከ ምሽት መጾሙን ነው፡፡ ይህም «አድልው ለጾም፤ ለጾም አድሉ፡፡» እንዲሉ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ቢጾም የሚያከራክር ወይንም ስህተት ነው የሚያሰኝ አለመሆኑን መረዳት ይገባል፡፡

ነቢያት ይወርዳል፣ ይወለዳል ብለው የተናገሩት ቃል ይፈጸም ዘንድ የሰው ልጆችም ድኅነት ማረጋገጫ እውን ይሆን ዘንድ እንደ ጾሙ እንደ ጸለዩ በልደቱም እንስሳት፣ ሰዎች እንዲሁም መላእክት በአንድነት በደስታ እንደዘመሩ የእኛም ደስታ የተረጋገጠበት ነው፡፡ በመሆኑም በፍቅር፣ በጾም በጸሎት ዛሬም እናስበዋለን፡፡ ነቢያት በረከት እንዳገኙ እኛም ከእግዚአብሔር በረከት እናገኛለን፡፡ ለዚህም አምላካችን ይርዳን አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፣ማህበረ ቅዱሳን መካነ ድር

የጥምቀት በዓል

የጥምቀት በዓል ከዘጠኙ የጌታ ዐበይት በዓላት መካከል አንዱ ነው።  በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እምነትና ስርዓት አክብሮት መሰረት በየዓመቱ ከጥር ፲ እስ ከ ጥር ፲፩ ቀን በደማቅ ስነ ስርዓት በካህናት፣በምዕመናን በሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ይከበራል። በዓሉ የሚከበረው ጌታ በዕደ ዮሐንስ በማየ ዮርዳኖስ የተየመቀበት ምስጢረ ጥምቀትና ሥርዓተ ጥምቀትን የመሰረተበት ዕለት በመሆኑ ነው። ጌታ የተጠመቀው በተወለደ በሠላሳኛው ዓመት ሲሆን ያ ወራት ዮሐንስ መጥምቁ ሕዝቡን እየሰበሰበ የሚያጠምቅበት ጊዜ ነበር።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በአደባባይ ከምታከብራቸው ታላላቅ በዓላት አንዱ የሆነው በዓለ ጥምቀት በተለይ በአዲስ አበባ ጃንሜዳ፣ በጐንደር ፋሲለደስ ባሕረ ጥምቀት፣ በአክሱም ማይሹም ባሕረ ጥምቀት፣ በደብረ ሮሃ ቅዱስ ላሊበላ ዮሐንስ አምባ ገጠርጌ ባሕረ ጥምቀትና በመላው ኢትየጵያ በዋዜማው የዮርዳኖስ ምሳሌ የሆነ ባሕር ካለበት ዘንድ ሄደው ለማደር ካህናቱና ምእመናኑ ከየአብያተ ክርስቲያናቱ ሲወጡ ሃይማኖታዊ ሥርዓቱና ጣዕመ ዝማሬው ለኦርቶዶክሳዊያኑ ብቻ ሳይሆን በቤተክርስያናችን ሥርዓተ አምልኮና በበዓል አከባበራችን ተስበው ወደ ሀገራችን ለሚመጡት ታዳሚዎች፣ እንግዶችና ቱሪስቶች ጭምር የደስታን ስሜት የሚፈጥር ነው፡፡

በየጥምቀት ባሕሩ ዙሪያ ሰፍረው ድምፀ ይባቤውን ከድምፀ ዝማሬው ጋር አንድ በማድረግ ሲያመሰግኑና ሲዘምሩ የሚያድሩት ሊቃውንቱ፣ ሥርዓተ ቅዳሴውን በማከናወን ለተልእኮ ምስጢር (ለሠሪዐ ቁርባን) የሚተጉት ቀሳውስቱና ዲያቆናቱ ምእመናኑና ምእመናቱ በረከት የሚያስገኘውን የባሕረ ጥምቀቱን ሥርዓት በመፈጸም በተዋሕዶ ሃይማኖት አንድነት ያላቸውን የክርስቶስ ማኅበርና ቤተሰብ መሆናቸውን በእንደዚህ ያለሃይማኖታዊ ሥርዓት ይገልጹታል፡፡

ሥርዓተ ቅዳሴው ከተፈጸመ በኋላ ሲነጋ በወንዙ ዳር (በግድቡ) ጸሎተ አኮቴት ደርሶ፣ አራቱ ወንጌላት ተነበው ባሕረ ጥምቀቱ ተባርኮ ለተሰበሰበው ሕዝብ ይረጫል፡፡ ታቦተ ሕጉ ከመነሣቱ በፊት “ኃዲጎ ተስዓ ወተስዓተ ነገደ ቆመ ማዕከለ ባሕር ገብዓ ወወጽአ በሰላም” የሚለውን ግሥ (መዝሙር) በየባሕረ ጥምቀቱ ዘምረው ታቦቱን አክብረው (አንሥተው) በሚያደርጉት የምስጋና ጉዞ የበዓሉ ደስታ ምድርን ይሞላታል፡፡

በእኛ ላይ የነበረውን በትእዛዛት የተጻፈውን የዕዳ ጽሕፈት ደመሰሰ (ቆላ 2፡14) የሚለውን ሐዋርያዊ ቃለ ስብከት በማስታወስ ከመጀመሪያ በዓይን ያዩት በኋላም እነርሱ የተኩት የቃሉ አገልጋዮች የሆኑት አባቶቻችን ብሔር፣ ቋንቋና ባህል ሳይለያያቸው የበዓላቱን ቀኖና አክብረው ሃይማኖታቸውን ጠብቀው በጥቂቱ በመታመን በብዙ ላይ ተሹመው ወደ ጌታቸው ደስታ ገብተዋል፡፡ ማቴ 25፡21 (ሉቃ 1፡1-4)

ስለሆነም ተዝካረ ጥምቀቱን (የጥምቀቱን መታሰቢያ) በዓል እንደ ጥንታውያኑ አባቶቻችን መሠረቱ ሳይናወጥ ሃይማኖታዊ ሥርዓቱ ሳይፋለስ ጸንቶ አንዲኖር ሁላችንም የድርሻችንን መወጣት ይገባናል፡፡


ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፦አቡነ ሳሙኤል ብሎግ

የነነዌ ጾም

የነነዌ ጾም ከሰባቱ የቤተክርስቲያን አጽዋማት አንዱና በየዓመቱ ከዐቢይ ጾመ  ፲፭ ቀን ቀድሞ ከሰኞ እስከ ረቡዕ የሚጾም ጾም ነው። የዐቢይ ጾም ማዘጋጃ ደወልም ተደርጎ ይወሰዳል። ይህ ጾም የነነዌ ሰዎችን የንስሐ ህይወት በማስታወስ የሚጾም ጾም ነው፡፡ ራሱ ጌታችንም የነዌ ሰዎችን የንስሐ ታሪክ በመጥቀስ አይሁድን ገስጾበታል፤በፍርድ ቀንም በዚያ ትውልድ ዘንድ እንደሚፈርዱበት ተናግሯል፡፡

 

"የነነዌ ሰዎች በፍርድ ቀን ከዚህ ትውልድ ጋር ተነስተው ይፈርዳሉ ፤ በዮናስ ስብከት ንስሐገብተዋልና፡፡" (ማቴ ፲፪፥፵፩) ፡፡ ይህንን የተናገረው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ጌታችን ለዚህ ትምህርቱ መነሻያደረገው የጻፎችን እና የፈሪሳውያንን ጥያቄ ነው፡፡ "መምህር ሆይ ከአንተ ምልክት ልናይእንወዳለን" ቢሉት "ክፉና አመንዝራ ትውልድ ምልክት ይሻል ፤ ከነቢዩም ከዮናስ ምልክት በቀር ምልክት አይሰጠውም ። ዮናስ በአሳ አንበሪ ሆድ ሦስት ቀንና ሌሊት አንደነበረ የሰው ልጅም በምደር ልብ ሦስት ቀንና ሌሊት ይሆናል፡፡የነነዌ ሰዎች በፍርድ ቀን ከዚህ ትውልድ ጋር ተነስተው ይፈርዳሉ ፤ በዮናስ ስብከት ንስሐ ገብተዋልና፡፡ እነሆ ከዮናስ የሚበልጥ ከዚህ አለ" ብሏቸዋል፡፡(ማቴ ፲፪፥፵፩)። 

ዐቢይ ጾም

በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ባሕልና ትውፊት መሠረት ከሰባቱ አጽዋማት አንዱና ዋነኛውየዐብይ ጾም ነው።ይህ ጾም ጌታ ከተጠመቀ በኋላ የጾመው የአርባ ቀን ጾም ነው፡፡ ምእመናን ጌታቸው ያደረገውን ምሳሌ ተከትለው ይጾሙታል፡፡

ይህ ዐቢይ ጾም ስምንት ሳምንታት፣ 56 ቀኖች አሉት፡፡ ከነዚህ ቀኖች ውስጥ ሰባት ቅዳሜ፣ ስምንት እሑድ ይገኛሉ፡፡ ዐሥራ አምስት ቀናት ማለት ነው፡፡ ከጥሉላት እንጂ ከእህል ውኃ ስለማጾሙ የጾሙ ወራት 40 ቀን ብቻ ነው፡፡ ይህም በጥንቷ ቤተ ክርስቲያን የነበረ ሥርዓት ነው፡፡ ለምሳሌ በ384 ዓ.ም ገደማ ከእስፓን ወደ ኢየሩሳሌም ቅዱሳት መካናትን ለመሳለም ረጅም ጉዞ ያደረገችው ኤጌሪያ የተባለች ሴት ‹‹የተሳላሚ ጉዞ›› (Peregrination ed loca Sancta) በሚለው መጽሐፏ የጥንት ክርስቲያኖች በዚህ አቆጣጠር ሲጠቀሙ ማየቷን ጽፋለች፡፡ የቆጵሮሱ ኤጲስ ቆጶስ ኤጲፋንዮስም በዚህ አቆጣጠር ይቆጥር ነበር፡፡ ሌሎች ደግሞ የመጀመሪያውንና የመጨረሻውን ሳምንት ለይተው ይቆጥራሉ፡፡ ለምሳሌ ሳምንት ጾመ ሕርቃል ይባላል፡፡ ሕርቃል (ኢራቅሊዮስ) የቢዛንታይን ንጉሥ ነበር፡፡ ይህ ሳምንት በስሙ የተጠራበትም ምክንያት የሚከተለው ነው፡፡

  

በዘመኑ ፋርሶች ኢየሩሳሌምን ወርረው፣ የጌታን መስቀል ማርከው ወስደው ነበር፡፡ እርሱ ወደ ፋርስ ዘምቶ መስቀሉን ከነርሱ ነጥቆ ይዞ ወደ ኢየሩሳሌም ተመልሷል፡፡ በዚህ ምክንያት ክርስቲያኖች ተደስተው ለስሙ መታሰቢያ ይህን የጾም ሳምንት በቀኖና ውስጥ አስገቡለት እየተባለ ይነገራል፡፡ ግሪኮች ግን ጾመ ሕርቃል የሚባለውን ነገር አያውቁም፡፡ ነገር ግን በዚህ ሳምንት ከዕንቁላልና ከአይብ ከዓሣ በቀር ሥጋ አይበላም ክልክል ነው ይላሉ፡፡ ጾም መሆኑንም ይናገራሉ፡፡ ዕንቁላል፣ አይብና ዓሣ መብላታቸውም በተድላ ደስታ የሰነበተ ሰውነት ወዲያው በጾም ሲደርቅ በሽታ እንዳያመጣባቸው ለጥንቃቄ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ የሳምንቱንም ስም ‹‹የአይብ ሳምንት ወይም ነጭ ጾም›› ይሉታል፡፡ የመጨረሻው ሳምንት ሕማማት ነው፡፡ ሐዋርያት የጌታችንን መከራ ሞት እያሰቡ የጦሙት ነው ይላሉ፡፡ ያም ሆነ ይህ ሁሉም ከዐቢይ ጾም ጋር እንደ መርገፍና እንደ እጀታ ስለተያያዘ ከዐቢይ ጾም ይቆጠራል፡፡

በዐቢይ ጾም ውስጥ የሚገኙት እሑዶች መጠሪያ ስሞችም የሚከተሉት ናቸው፤

የመጀመሪያው ሳምንት (እሑድ) – ዘወረደ

ሁለተኛው ሳምንት (እሑድ) – ቅድስት

ሦስተኛው ሳምንት (እሑድ) – ምኵራብ

አራተኛው ሳምንት (እሑድ) – መጻጕዕ

አምስተኛው ሳምንት (እሑድ) – ደብረ ዘይት

ስድስተኛው ሳምንት (እሑድ) – ገብር ኄር

ሰባተኛው ሳምንት (እሑድ) – ኒቆዲሞስ

ስምንተኛው ሳምንት (እሑድ) – ሆሣዕና

የፋሲካ በዓል የሚከበርበት የመጨረሻው የዐቢይ ጾም እሑድ ደግሞ ትንሣኤ ወይም ፋሲካ ይባላል፡፡

 

 

ይህ ታላቅ የሆነው የጾማችን ወራት በተለያየ ስያሜ  ይጠራል፡፡

 

1. ዐቢይ ጾም ይባላል፡፡

ሌሎች አጽዋማት ከቅዱሳን አበው የወረስናቸው የኑሮአቸው ፍሬዎች (ዕብ.13$7) ሲሆኑ ይኼኛው ግን በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የተመሠረተ በመሆኑ ዐቢይ (ታላቅ) ይባላል፡፡ 

 

2. ጾመ ሁዳዴ ይባላል፡፡

ሁዳድ ማለት የመንግሥት መሬት፣ የመንግሥት ርስት ማለት ነው፡፡ የመንግሥት ሁዳድ በሚታረስበት ጊዜ፣ አዝመራው በሚሰበሰብበት ጊዜ ልጅ ዐዋቂ ሳይባል የመንግሥቱ ዜጋ ሁሉ ለሥራ ታጥቆ እንደሚነሣ ይህንንም የጌታ ጾም የጌታ ወይም የጌታ ሁዳድ የክርስቶስ ዜጎች የሆኑ ምእመናን ሁሉ ይጾሙታልና ጾመ ሁዳዴ ይባላል፡፡

 

3. የካሣ ጾም ይባላል፡፡

አባታችን አዳምና እናታችን ሔዋን ከገነት የተባረሩት ለውርደት ሞት$ ለሲዖል ባርነት የበቁት በመብል ምክንያት ነበር፡፡ በሆዳምነቱ የወደቀውን የሰው ልጅ በፈቃዱ በጾመው ጾም ካሠው$ እንዲሁም አዳም ከገነት ሲባረር ረሃበ ጸጋ (መንፈሳዊ ረሃብ) ደርሶበት ነበርና ረሃቡን በረሃብ ካሠለት፡፡ የኛን ረሃብ እርሱ ተራበ፡፡

 

4. የድል ጾም ይባላል፡፡

ጌታችን ተጠምቆ ዕለቱን ወደ ገዳመ ቆሮንቶስ በመሔድ ከሰው ተለይቶ አርባ መዓልትና አርባ ሌሊት በመጾም አዳምና ሔዋንን በመብል የረታቸውን ዲያብሎስን እርሱ ድል አደረገላቸው፡፡ ዲያብሎስን ድል ያደርግ ዘንድ ከዚህ ዓለም ርቆ ወደ ገዳም መሄዱ አዳም ከዚህ ዓለም ርቃ በምትገኘው ገነት ድል ሆኖ ነበርና እርሱም ዲያቢሎስን በገዳም$ በዚህ ዓለም ርቆ ድል አደረገልን ለእኛም ፈቃደ ሥጋችንን የምናሸንፍበተ ኃይል ሰጠን፡፡ ይህ ጾም ጠላት ዲያቢሎስ የተሸፈነበት ነው፡፡

 

5. የመሸጋገሪያ ጾም ይባላል፡፡

ሊቀ ነቢያት ሙሴ ሕዝቡን ከሕገ ልቡና ወደ ሕገ ኣሪት ሲያሸጋግር አርባ መዓልትና ሌሊት በደብረ ሲና እንደ ጾመው ሁሉ ጌታችንም እኛን ከሕገ ኦሪት ወደ ሕገ ወንጌል ሲያሸጋግረን አርባ መዓልትና ሌሊት ጾመ፡፡ ስለዚህም የመሸጋገሪያ ጾም እንለዋለን፡፡

 

6. ጾመ አስተምህሮ ይባላል፡፡

ሁሉን ነገር በቅጽበትና ያለ ድካም ማድረግ የሚችለው አምላክ እኛን ልጆቹን ያስተምረን ዘንድ ራሱን ዝቅ አደረገ፡፡ መልካም መምህር ተማሪዎቹ

 

ይገባቸው ዘንድ ዝቅ ብሎ በነርሱ ቋንቋ እየተናገረ በሚችሉት እየመሰለ እንዲያስረዳ ጌታችንም እኛን ወደርሱ ይወስድ ዘንድ አስቀድሞ እርሱ ወደ እኛ መጣ፡፡ ረሃባችንን ተራበ$ ድካማችንን ደከመ$ ፈተናችንን ተፈተነ ለእኛም አርአያ ሆኖ ትሕትናን$ ትዕግሥትንና ፈተናን በጾም ማሸነፍን አስተማረን፡፡

 

7. የቀድሶተ ገዳም ጾም ይባላል፡፡

እነ መጥምቁ ዮሐንስ እነ ነቢዩ ኤልያስ የኖሩትን የብሕትውና ኑሮ ጌታ ባርኮ ሰጠን፡፡ ከከተማ ወጥቶ ከሰው ርቆ በበረሃ ከአራዊት ጋር እየኖረ በዲያብሎስ ተፈትኖ ድል አደረገ፡፡ ዛሬም ልጆቹ በየገዳማቱ ድምፀ አራዊትን ግርማ ሌሊትን ተግሠው ዓለምን ንቀው$ ከሰው ርቀው በጾም በጸሎት ከአጋንንት ጋር ይታገላሉ$ ድልም ያደርጋሉ፡፡

 

8. የመዘጋጃ ጾም ይባላል፡፡

ለእሥራኤላውያን ስለ በዓለ ፋሲካ አከባበር ሲነገራቸው የፋሲካውን በግ ሥጋ ከመራራ ቅጠል ጋር እንዲበሉት ታዘው ነበር (ዘጸ.12$18)፡፡ ይኽም መራራ ቅጠል በግብፅ ይኖሩት የነበረውን የመከራ ኑሮ የሚያሳስባችውና ደግም ወደ ግብፅ (ምድረ ፋይድ) እንዳይመለሱ ከኃጢአተ ይርቁ ዘንድ የሚያስተምራቸው ነበር፡፡ የፋሲካው በግ ደግሞ እግዚአብሔር በፍቅሩ የሰጣቸውን ነፃነት ያሳስባቸዋል፡፡

 

ዛሬም በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከበዓለ ትንሣኤው በፊት የጾም ወራት ያስቀደምነው ለዚህ ነው፡፡ ከመብል ስንከለከል ለአዳምና ሔዋን የተሰጠውን ሕግ እናስባለን$ ረሃብ ሲሰማን በሰው ልጅ ላይ ደርሶ የነበረው የጸጋ ረሃብ$ የመንፈስ ረሃብ ይታወሰናል$ ስንደክም ስንጐሰቁል በአዳምና ሔዋን የደረሰው የመንፈስ ጉስቁልና$ የበደልን የዕዳ ቀንበር ተሸክመው የደረሰባቸው ድካም ይታሰበናል፡፡ እኛም በነርሱ የደረሰችው ሞት በእኛ እንዳትደርስ ዳግም ወደ ኃጢአት እንዳንመለስ ይመክረናል ያሳስበናል፡፡

 

በጾሙም መጨረሻ የሐዲስ ኪዳንን በግ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሥጋና ደም እንቀበላለን፡፡ ያን ጊዜም ሞትን ካሸነፈው አምላክ ጋር አንድ እንሆናለን (ዮሐ.6$55-58)፡፡ ሞታችን በሞቱ እንዳለፈ እናስባለን (1ቆሮ.11$26)፡፡ በመሆኑም ይህ ወቅት በዓለ ትንሣኤ- የሐዲስ ኪዳን ፋሲካን ለማክበር$ ሥጋ ወደሙን ለመቀበል ራሳችንን የምናዘጋጅበት የምንፈትንበት ነው (1ቆሮ.11$27)፡፡

 

9. የሥራ መጀመሪያ ጾም ነው፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የማስተማር ሥራውን ከመጀመሩ$ የመንግሥተ ሰማያትን አንቀጽ ከማስተማሩ በፊት በገዳመ ቆሮንቶስ አርባ መዓልትና ሌሊት ጾመ፡፡ ይህም ለእኛ የማንኛውም ነገር መጀመሪያው ጾም መሆኑን ሲያሰተምረን ነው፡፡ ለዚህም ነው ሐዋርያት ጾምን የሥራቸው መጀመሪያ ያደረጉት፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፣ማኅበረ ቅዱሳን አሜሪካ ማዕከል

ደብረ ዘይት

በቤተክርስቲያናችን ሕግና ሥርዓት መሠረት የዓብይ ጾም እኩሌታ ደብረ ዘይት በመባል ተሰይሟል፤ ይኽውም በዚሁ ሰንበት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ሆኖ ለቅዱሳን ሐዋርያቱ ስለዓለም ጥፋትና ስለዳግም ምጽአቱ ምልክቱን የነገረበትን የምናስብበት ቀን ነው።። ይኸውም /ማቴ. ፳፬፥ ፫-ፍ/ እንደተገለጸው፤

  • ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉና ብዙዎችንም ያስታሉ

  • ጦርነትን የጦርነትንም ወሬ ትሰማላችሁ

  • ሕዝብ በሕዝብ ላይ፣ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሣሉ

  • በየሀገሩም ረኃብ፣ ቸነፈርም፣ የምድር መናወጥም በልዩ ልዩ ስፍራ ይሆናል

  • በዚያን ጊዜ ለመከራ አሳልፈው ይሰጧችኋል፤ ይገድሏችሁማል፤ ስለ ስሜም በሕዝብ ሁሉ ዘንድ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ

  • በዚያን ጊዜም ብዙዎች ይሰናከላሉ እርስ በእርሳቸውም አሳልፈው ይሰጣጣሉ፣ እርስ በእርሳቸውም ይጣላሉ

  • ብዙዎች ሐሰተኞች ነቢያትም ይነሣሉ፤ ብዙዎችንም ያስታሉ

  • ከዐመፅም ብዛት የተነሣ የብዙ ሰዎች ፍቅር ትቀዘቅዛለች

  • የጥፋት ርኩሰት በተቀደሰችው ሥፍራ ቆሞ ታያላችሁ

  • በዚያን ጊዜ ከዓለም መጀመሪያ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ያልሆነ እንግዲህም  ከቶ የማይሆን ታላቅ መከራ ይሆናል ካለ በኋላ

  • እስከመጨረሻ የሚጸና ግን እርሱ ይድናል በማለት ገልጾላቸዋል።

ክብር ምስጋና ይግባውና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ ለልጆቹ ካለው ፍቅር የተነሳ ሁልጊዜም የምንድንበትን መንገድ ሳያሳውቀን ቀርቶ አያውቅም። አሁንም ከላይ የተዘረዘሩትን የመሰናከያ አይነቶችና የመከራ ብዛቶችን ብቻ ጠቅሶ አላለፈም። ይልቁንም ጭንቅ ሲመጣ ማቅለያውን፣ መከራ ሲገጥም መውጫውን፣ ፈተና ሲከብደን ማለፊያውን ጭምር አሳይቶናል፣ ነግሮናል።

ደብረ ዘይት ማለት ቃሉ “ደብር” ሲል ተራራ ሲሆን “ዘይት” ሲል የወይራ ዛፍን ያመለከታል። ባጠቃላይ ደብረ ዘይት የወይራ ዛፍ (የዘይት ዛፍ) የበዛበት ተራራ ማለት ነው። ቦታው በቅድስት አገር ኢየሩሳሌም ከጎለጎታ (ቀራንዮ) ተራራ በስተምስራቅ በግምት ፪ ኪሎሜትር ርቀት ላይ የሚገኝ ታላቅ ተራራ ነው። በሁለቱ ተራሮች መካከል ጌቴሴማኒ የሚባለው ለምለም ስፍራ ይኸውም የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም የመቃብር ስፍራ ይገኛል።

ሆሣዕና

ሆሣዕና ቃሉ የዕብራይስጥ ሲሆን ትርጉሙም አሁን አድን ማለት ነው። በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት መሠረት የታላቁ ዓቢይ ጾም ስምንተኛ እሑድ የሆሣዕና በዓል በድምቀት የሚከበርበት ዕለት ነው። በዚህ ዕለት ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በታላቅ ትህትና በአህያ ጀርባ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ያደረገውን ጉዞ የሚዘክር ቃለ እግዚአብሔር በስፋት ይደርሳል። በአራቱም ወንጌላውያን በቅዱስ ማቴዎስ፣ ማርቆስ፣ ሉቃስና፣ ዮሐንስ ይህንኑ የፍጹም ትህትና እና የፍቅር ጉዞ አስመልክቶ የተጻፉ የወንጌል ክፍሎች  (ማቴ 21፥1-17 ፣ ማር 11፥1-10 ፣  ሉቃ 19፥28-44 ፣ ዮሐ 12፥9-19) በቅድስተ ቤተ ክርስቲያን ዑደት እየተደረገ በአራቱም አቅጣጫዎች ይነበባሉ።

ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከቅዱሳን ሐዋርያት ጋር ወደ ኢየሩሳሌም ባደረገው ጉዞ ቢታንያና ቤተ ፋጌ አካባቢ ሲደርሱ ከደቀ መዛሙርቱ ሁለቱን እንዲህ አላቸው ”በፊታችሁ ወዳለችው መንደር ሂዱ፥ በዚያን ጊዜም የታሰረች አህያ ከውርንጫዋ ጋር ታገኛላችሁ፤ ፈትታችሁ አምጡልኝ ማንም አንዳች ቢላችሁ ጌታቸው ይሻቸዋል በሉ፤ ወዲያውም ይሰዱአችኋል” (ማቴ 21፥2-3)። እነርሱም ለምን እና እንዴት ሳይሉ ያለ አንዳች ጥያቄ በፊታቸው ወዳለው መንደር ተጉዘዋል። እርሱ ቀድሞ የነበረውን፣ አሁንም ያለውን፣ ወደፊትም የሚኖረውን የሚያውቅ አምላክ መሆኑን ተረድተዋልና። የታዘዙት ደቀመዛሙርት ጌታ እንደነገራቸው በመንደሩ የታሰረች አህያ ከነውርንጫዋ አግኝተው እንደታዘዙት ማሰሪያዋን ሲፈቱ ባለንበረቶቹ ወጥተው ለምንድን ነው? ብለዋቸዋል። ”እነርሱም እንደታዘዙት ለጌታ ያስፈልጉታል አሉ”። እውነት ነው እርሱ እግዚአብሔር ነውና የፈለገውን ለመከልከል የሚቻለው ማንም የለም። እናም ባለቤቶቹ ያለማጉረምረም ለጌታ የሚያስፈልገውን ሰጡ። ደቀ መዛሙርቱ ከእስር የፈቷቸውን አህያና ውርንጫ ወደጌታ አመጡ እርሱም በአህያ ጀርባ ተቀመጠ።

የጌቶች ጌታ የንጉሦች ንጉሥ የሆነ አምላካችን፥ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዓለምን ለማዳን ወደዚህ ዓለም ሲመጣ ራሱን ዝቅ አድርጎ በቤተልሔም በከብቶች በረት እንደተገኘ ሁሉ በአህያ ጀርባ ተቀመጠ። ይህ ለአንዳንዶች እንደመሰላቸው በአጋጣሚ የተደረገ ሳይሆን ቀደም ብሎ በብሉይ ኪዳን በመንፈስ ቅዱስ መሪነት በነቢዩ ዘካርያሰ ትንቢት የተነገረለት አምላካዊ ምስጢር ነው። ”አንቺ የጽዮን ልጅ ሆይ፥ እጅግ ደስ ይበልሽ፤ አንቺ የኢየሩሳሌም ልጅ ሆይ፥ እልል በዪ፤ እነሆ፥ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው፤ ትሑትም ሆኖ በአህያም፥ በአህያይቱ ግልገል በውርንጫይቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል” (ዘካ 9፥9)። እንኳን ፈሪሳውያኑና ሕዝቡ፥ አብረውት የነበሩ ቅዱሳን ሐዋርያት እንኳን ይህ ስለ እርሱ እንደተነገረ የተረዱት እርሱ በመስቀል ላይ ከከበረ በኋላ ነው። ”ደቀ መዛሙርቱም ይህን ነገር በመጀመሪያ አላስተዋሉም፤ ነገር ግን ኢየሱስ ከከበረ በኋላ በዚያን ጊዜ ይህ ስለ እርሱ እንደ ተጻፈ ይህንም እንዳደረጉለት ትዝ አላቸው” እንዲል (ዮሐ 12፥16)። በትርጓሜ ወንጌል አህያዋና ውርንጫይቱ ምሳሌነትም አላቸው:- ቀድሞ አባቶች ነቢያት ዘመነ ጸብ የሆነ እንደሆነ በፈረስ ተቀምጠው፣ ዘገር ነጥቀው ይታያሉ። ዘመነ ሰላም የሆነ እንደሆነ በአህያ ተቀምጠው መነሳንስ ይዘው ይታያሉ። አምላካችንም እንደ ከበሩ ነገሥታት ሥርዓት በተንቆጠቆጠ  ሰረገላና በፈረስ ሳይሆን በአህያ ውርንጫ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም መግባቱ መንግሥቱ የሰላምና የፍጹም ትህትና መሆኗንና ሁሉም ሰው ተገዶ እና ፈርቶ ሳይሆን በፈቃዱ የሚገባባት መሆኗንም ለማሳየት ነው። አንድም:- ውርንጫይቱ ቀድሞ ምንም ጭነት የማያውቃቸው ሕግን ያልተቀበሉ በሕግ ያልኖሩ አሕዛብ ምሳሌ ስትሆን፣ ጭነት የለመደች አህያይቱ ደግሞ ሕግና ሥርዓት ተሰርቶላቸው የነበሩ የእስራአል ምሳሌ ናት። ኪሩቤል ዙፋኑን የሚሸከሙለት እርሱ ራሱን ዝቅ አድርጎ በተናቀች እንሰሳ ላይ መቀመጡ ዕጹብ ድንቅ ነው!

በዚያን ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ ልብሳቸውን እያወለቁ በአህያዪቱ ላይ ጎዘጎዙለት። ”ከሕዝቡም እጅግ ብዙዎች ልብሳቸውን በመንገድ ላይ አነጠፉ” (ማቴ 21፥8)። መንፈስ ቅዱስ ክብሩን የገለጠላቸው ሕፃናትና ሌሎችም ብዙዎች የድል ማብሠሪያ ወይም የድል አድራጊነት ምልክት የሆነውን የዘንባባ ዝንጣፊ እየጎዘጎዙና እልል እያሉ ሆሣዕና በአርያም በጌታ ስም የሚመጣ የእስራኤል ንጉሥ የተባረከ ነው እያሉ ተቀበሉት። ዮሐ 12፥12-13። የጨለማውን ኃይል በሞቱ ድል የሚነሣ እውነተኛ ድል አድራጊ ንጉሥ ነውና መንፈስ ቅዱስ መርቷቸው የዘንባባ ዝንጣፊን ይዘው ተቀበለውታል። በሰው እይታ ምንም አያውቁም የተባሉ ለጋ ሕፃናት የእግዚአብሔር መንፈስ እየመራቸው ”ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ እያሉ እየጮሁ ዘመሩለት”። ጌታችን በፍጹም ትህትና በከብቶች በረት በቤተልሔም በተገኘ ጊዜ ቅዱሳን መላእክት እመቤታችንን እና ልጇን ከበው ያመሰገኑትን ምስጋና ደቀ መዛሙርቱም በትህትና በአህያ ጀርባ ላይ በተቀመጠ ጊዜ ደግመው ”በሰማይሰላምበአርያምምክብር ይሁን”እያሉአቀረቡለት። ሉቃ 19፥37-38። እርሱ የተወለደው ለሰላም ነውና መንፈስ ቅዱስ ባወቀ በታላቅ ድምጽ እንደ ልደቱ ቀን ሁሉ ቅዱሳን ሐዋርያቱ ”በሰማይ ሰላም በአርያምም ክብር” አሉ ግሩም ድንቅ  ነው!

በሰማይ ያለ ዕረፍት የሚመሰገን ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር ተገኝቶ የሕፃናቱን፣ የደቀ መዛሙርቱንና የሕዝቡን ምስጋና ተቀበለ። በዚህ ታለቅ ምስጋና ወደኢየሩሳሌም ሲቃረብ ከምስጋናው ድምጽና ከእርሱም ግርማ የተነሳ ”መላው ከተማ ይህ ማን ነው? ብሎ ተናወጠ” (ማቴ 21፥10)። እርሱማ ቅድመ ዓለም የነበረ፣ አሁንም ያለ፣ ዓለምንም አሳልፎ ለዘለዓለም በመንግሥቱ የሚኖር አምላክ ወልደ አምለክ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ሕፃናቱ ደቀ መዛሙርቱና ሕዝቡ የዘንባባ ዝንጣፊ ይዘው፣ ልብሳቸውን አውልቀው በመንገዱ እያነጠፉለት ”አቤቱ እባክህ አሁን አድን፥ ሆሣዕና በአርያም” እያሉ ሲዘምሩ የካህናት አለቆች፣ ጻፎችና ፈሪሳውያን ብስጭታቸውን መቆጣጠር አልተቻላቸውም። ይህም በንግግራቸው ይታወቃል፥- ”ነገር ግን የካህናት አለቆችና ጻፎች ያደረገውን ድንቃ ድንቅ በመቅደስም ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ እያሉ የሚጮኹትን ልጆች ባዩ ጊዜ፥ ተቈጥተው እነዚህ የሚሉትን አትሰማምን? አሉት። ኢየሱስም፥- እሰማለሁ፤ ከሕፃናትና ከሚጠቡት አፍ ምስጋናን ለራስህ አዘጋጀህ የሚለውን ቃል ከቶ አላነበባችሁምን? አላቸው”። ማቴ 21፥15-16። መዝ 8፥2። በሌላም ሥፍራ ”ከሕዝብም መካከል ከፈሪሳውያን አንዳንዱ:- መምህር ሆይ፥ ደቀ መዛሙርትህን ገሥጻቸው አሉት። መልሶም:- እላችኋለሁ፥ እነዚህ ዝም ቢሉ ድንጋዮች ይጮኻሉ አላቸው” (ሉቃ 19፥ 39-40)። ይህም መልስ ትንቢቱ ይፈጸም ዘንደ ግድ ነውና አይሆንላችሁም የሚል ነው። የካህናት አለቆች፣ ጻፎችና ፈሪሳውያን ጥረት ምስጋናው እንዲቋረጥ ነበር አልሆነላቸውም እንጂ።

ጌታችን ኢየሩሳሌም መግቢያ ላይ ሲደርስ ከተማይቱን አይቶ እንዲህ እያለ አለቀሰላት:- ”ለሰላምሽ የሚሆነውን በዚህ ቀን አንቺስ ስንኳ ብታውቂ፤ አሁን ግን ከዓይንሽ ተሰውሮአል ወራት ይመጣብሻልና፥ ጠላቶችሽም ቅጥር ይቀጥሩብሻል ይከቡሻልም በየበኵሉም ያስጨንቁሻል፤ አንቺንም በአንቺም ውስጥ የሚኖሩትን ልጆችሽን ወደ ታች ይጥላሉ፥ በአንቺ ውስጥም ድንጋይ በድንጋይ ላይ አይተዉም፥ የመጐብኘትሽን ዘመን አላወቅሽምና” (ሉቃ 19፥41-44)። እርሱ ሁሉን የሚያውቅ ነውና ከተማይቱ የሰላም ንጉሥን አሳልፎ በመስጠት የምታጣውን ሰላምና የሚከተላትን ቅጣት ያውቃልና እንባውን አፈሰሰላት። ዕለተ ሆሣዕና ይህ ሁሉ እውነት የሚዘከርባት ታላቅ ዕለት ናት።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፦ማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓ ማእከል

ሰሙነ ሕማማት

ሰሙነ ሕማማት ሰሙነ ስቅለትም ይባላል፡፡ ይኸውም ከሆሣዕና ማግስት (ከሰኞ) ጀምሮ እስከ ዓርብ ስቅለት ያለው ክፍለ ጊዜ ሲኾን ይህም ከጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዐበይት በዓላት መካከል አንዱ ነው፡፡ ‹‹እርሱ ግን በእውነት ደዌያችንን ተቀበለ፤ ሕማማችንንም ተሸከመ፡፡ ስለ እኛም ታመመ፡፡ እኛም እንደ ታመመ፣ እንደ ተገረፈ ቈጠርነው፡፡ እርሱ ግን ስለ ኃጢአታችን ቈሰለ፤ ስለ በደላችንም ታመመ፡፡ የሰላማችንም ተግሣፅ በእርሱ ላይ ነበረ፡፡ በእርሱም ቊስል እኛ ተፈወስን፤›› በማለት ነቢዩ ኢሳይያስ እንደ ገለጸው (ኢሳ. ፶፫፥፬-፭)፣ ሰሙነ ሕማማት የክብርና የሥልጣን ዅሉ ባለቤት፣ ዅሉን ቻይ፣ ኃያል የኾነው አምላክ እኛን ከመውደዱ የተነሣ የእኛን ዕዳ ለመክፈል በመስቀል እስከ መሞት ድረስ እጅግ ከባድና አሰቃቂ የኾነ መከራ በፈቃዱ የተቀበለበት ሰሙን ከመኾኑም ባሻገር እኛ ፍጹም ድኅነትን ያገኘንበት ጊዜ ነው፡፡

ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን ወደ ጌቴሴማኒ ይዞ ከሔደ በኋላ ከእነርሱ ፈቀቅ ብሎ ‹‹ሰውነቴ እስከ ሞት ድረስ አዘነች፤›› እያለ ወዙ እንደ ውኃና እንደ ደም እስኪወርድ ድረስ እየወደቀ እየተነሣ በስግደት በኀዘን እንደ መሠረተው ዅሉ፣ የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተከታይ የኾነ ክርስቲያን በሙሉ በኀዘን፣ በለቅሶ እየሰገደ የፈጣሪውን ውለታ የሚያስብበት፤ ለፈጣሪው ያለውን ፍቅር የሚገልጥበት ወቅት ነው – ሰሙነ ሕማማት (ማቴ. ፳፮፥፴፰፤ ማር. ፲፬፥፴፬፤ ሉቃ. ፳፪፥፵፬)፡፡ ‹‹… ክርስቶስ ተሰቅለ በሥጋሁ በእንቲአነ ወአንትሙኒ ተወልተዉ በይእቲ ሕሊና እስመ ዘሐመ በሥጋሁ ድኅነ እምኃጣውኡ፤ ክርስቶስ ስለ እኛ በሥጋው ከተሰቀለ እናንተም ይህችን አሳብ ጋሻ አድርጋችሁ ኑሩ፡፡ በሥጋው መከራ የተቀበለ ከኃጢአት ድኖአልና፤›› በማለት ቅዱስ ጴጥሮስ አጥብቆ የመከረን ስለዚህ ነው (፩ኛ ጴጥ. ፬፥፩)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፣ማህበረ ቅዱሳን መካነ ድር

ዓርብ ስቅለት

ዓርብ ስቅለት የዕዳ ደብዳቤያችን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ለመጨረሻ ጊዜ የተደመሰሰበት፤ ከአጋንንት አገዛዝ ነጻ የወጣንበት ዕለት ስለኾነ ‹የድኅነት ቀን› ይባላል፡፡ ጌታችን ከተያዘባት ሰዓት አንሥቶ አይሁድ ከቀያፋ ወደ ሐና፣ ከሐና ወደ ቀያፋ ሲያመላልሱት አደሩ፡፡ ሲነጋ ከቀያፋ ወደ ጲላጦስ አደባባይ አስረው ወሰዱት (ማቴ. ፳፯፥፩-፶፯)፡፡ አይሁድ ይህን አጥፍቶአል የሚሉት ነጥብ ሳይኖራቸው ነውና ጌታችንን ለፍርድ ያቀረቡት ጲላጦሰ እነርሱ ወደ ተሰባሰቡበት ቦታ ወጥቶ ‹‹ይህን ሰው ወደ እኔ ያመጣችሁበት በደል ምንድን ነው?›› ሲል በጠየቃቸው ጊዜ በቂ ምላሽ አላቀረቡም፡፡

‹‹ክፉ የሠራ ባይኾንስ ወደ አንተ ባላመጣነውም ነበር›› በሚል የሸፍጥ ቃል ሲያጕረመርሙ ጲላጦስ መልሶ ‹‹እኔ ምንም ጥፋት አላገኘሁበትም፤ እናንተወስዳችሁ እንደ ሕጋችሁፍረዱበት፤›› አላቸው፡፡ አይሁድም ኦሪት ‹‹ኢትቅትል ብእሴ ጻድቀ ወኀጥአ ኢታኅዩ፤ ጻድቅን ሰው አትግደል፤ ኀጥኡንም ከፍርድአታድን፤›› ትላለችና ‹‹እኛስ ማንንም ልንገድልአልተፈቀደልንም፤›› ብለዋል (ዮሐ. ፲፰፥፳፰-፴፩)፡፡ ይኸውም መንፈስ ቅዱስ ‹‹በሕጋችን ጻድቀ ባሕርይክርስቶስን መግደል አይገባንም ሙሉ በሙሉ ጥፋተኞች ነን፤›› ሲያሰኛቸው ነው፡፡ በኋላም እርሱ ሞቶ ዓለም ይድን ዘንድ ወደ ምድር መጥቷልና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያለ ጥፋቱ ሞት ተፈረደበት፡፡ ስለዚህም ገርፈው ሰቀሉት፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፣ማህበረ ቅዱሳን መካነ ድር

ትንሳኤ

ትንሳኤ ማለት ተንሥአ ካለው የግዕዝ ግሥ የተወረሰ ሲሆን ትርጉሙም መነሣት አነሣሥ ማለት ነው ።እስራኤል ዘስጋ ያከብሩት የነበረው በዓለ ፋሲካ ከባርነት ቀንበር ወደ ነጻነት የተላለፉበት ከኀዘን ወደ ደስታ የተሸጋገሩበት በዓል ነበር ። የሐዲስ ኪዳን በዓለ ትንሣኤ ግን እሥራኤል ዘነፍስ ከኃጢአት ወደ ጽድቅ የተመለስንበት ከሐሳር ወደ ክብር ከአሮጌው ወደ ሐዲስ ሕይወት የተሸጋገርንበት መንፈሳዊ የነጻነት በዓል ነው ።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማየ ሰማያት ወርዶ ከድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ በከብቶች በረት ከተወለደበት ሰዓት ጀምሮ ለሰው ልጅ ድህነት ሲል ጽኑ መከራና ስቃይን ተቀብሏል። በተለይ በመጨረሻው ሰዓት ከሰው ልጅ አዕምሮ በላይ የሆነ ስቃይ፣ መከራ፣ እንግልትና ግርፋትን ተቀብሎ፤ በጲላጦስ ካለበደሉ ከወንበዴዎች ጋር ተፈርዶበት፤ በቀራንዮ አደባባይ በዕለተ አርብ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ፤ ነፍሱን በፈቃዱ ሰጥቶ አዳምንና ዘሩን ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን መልሶ በሦስተኛው ቀን መቃብር ክፈቱልኝ፣ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል ብርሃንን ተጎናጽፎ  በታላቅ ኃይልና ስልጣን በክብር ተነስቷል።

“እነሆም የጌታ መልአክ ከሰማይ ወረደ፣ ታላቅ የምድር መናወጥ ሆነ፣ እናንተስ አትፍሩ የተሰቀለውን ኢየሱስን እንድትሹ አውቃለሁና። እንደ ተናገረው ተነስቷልና በዚህ የለም ኑና እዩ አላቸው።” (ማቴ 28፥5)። የጌታ መልአክ ለእናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አምላክን እንደምትወልድ እንዳበሰራት ሁሉ እነሆ ጌታም ሞቶ በተቀበረ በሦስተኛው ቀን የትንሣኤውን ብስራት በሌሊት ወደ መቃብሩ ስፍራ ለመጡ የገሊላ ሰዎች ተናገረ።  ስለ አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ አስቀድመው ነቢያት በትንቢታቸው ተንብየዋል። ራሱ ጌታችንም በዘመነ ሥጋዌው በምሳሌ አስተምሯል። በመጨረሻም እንደተናገረ በተግባር ከመቃብር ተነስቷል። ሐዋርያት በስብከታቸው እና በመጽሐፋቸው ስለ ትንሣኤው ምስክርነት በመስጠት አረጋግጠው አስፍተውና አምልተው አስተምረዋል፤ ጽፈዋል። (ማቴ 28፣ ማር 16፣ ሉቃ 24፣ ዮሐ 20)። ነገር ግን ስለ ጌታችን ትንሣኤ በቅዱሳት መጻሕፍትም ሆነ ጌታችን ራሱ በትምህርቱ ግልጽ አድርጎ ቢናገርም ሰዱቃውያንና ሌሎች ብዙ ሰዎች ለማመን ያዳግታቸው ነበር። ከሐዋርያትም መካከል የሆነው ቅዱስ ቶማስ እንኳ ጌታችን በዝግ ቤት ሰላም ለእናንተ ይሁን ብሎ የተወጋውን ጎኑን አሳይቶ በክብር መነሣቱን እስከሚያረጋግጥለት ድረስ የጌታችንን ትንሣኤ ለማመን እንደተቸገረ ቅዱስ መጽሐፍ ይነግረናል። በተጨማሪም የጌታን ትንሣኤ እና ትንሣኤ ሙታንን በአጠቃላይ ለመቀበል የተቸገሩ ብዙዎች እንደነበሩ ከቅዱሳት መጻሕፍት እንረዳለን። 

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፦ማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓ ማእከል

ርክበ ካህናት

‹ርክብ› ወይም ‹ረክብ› የሚለው ቃል ‹ተራከበ፤ ተገናኘ› ከሚለው የግእዝ ግስ የወጣ ሲኾን፣ ትርጕሙም ማግኛ፣ መገኛ፣ መገናኛ ማለት ነው (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ገጽ ፰፻፴፩)፡፡ ‹ክህነት› የሚለው ስያሜም ከጵጵስና ጀምሮ እስከ ዲቁና ድረስ ያሉትን የቤተ ክርስቲያን መዓርጋት የሚያጠቃልል ቃል ሲኾን ካህን (ነጠላ ቍጥር)፣ ካህናት (ብዙ ቍጥር) በአንድ በኩል ቀሳውስትን የሚወክል ኾኖ በሌላ በኩል ደግሞ የጳጳሳት፣ የኤጲስ ቆጶሳት፣ የቀሳውስት፣ የዲያቆናት የጋራ መጠሪያ ነው፡፡ ‹ርክበ ካህናት› የሚለው ሐረግም የካህናት መገኛ፣ መገናኛ፣ ጉባኤ (መሰባሰቢያ)፣ መወያያ፣ ወዘተ የሚል ትርጕም አለው፡፡ በአጭሩ ‹ርክበ ካህናት› ማለት – የአባቶች ካህናት ማለትም የብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት (የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት) ጉባኤ ማለት ነው፡፡

በቅዱስ ዮሐንስ ወንጌል እንደ ተገለጸው ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሞት ከተነሣ በኋላ ለሦስተኛ ጊዜ ተገልጦ ከዐሥራ አንዱ ቅዱሳን ሐዋርያት ጋር ምሳ በልቷል፡፡ ከምሳ በኋላም ጌታችን ቅዱስ ጴጥሮስን ሦስት ጊዜ ጠርቶ ‹‹ትወደኛለህን?›› እያለ ከጠየቀው በኋላ እንደሚወደው ምላሽ መስጠቱን ተከትሎ በቅደም ተከተል ‹‹በጎቼን ጠብቅ፤ ጠቦቶቼን አሰማራ፤ ግልገሎቼን ጠብቅ፤›› በማለት የአለቅነት ሥልጣን ሰጥቶታል፡፡ ይህ ምሥጢር ለጊዜው ጌታችን ሐዋርያትን፣ ሰብዐ አርድእትንና ሠላሳ ስድስቱን ቅዱሳት አንስት በአጠቃላይ መቶ ሃያውን ቤተሰብእ እንዲጠብቅና እንዲከባከብ ቅዱስ ጴጥሮስን ማስጠንቀቁን፤ ለፍጻሜው ግን የቤተ ክርስቲያን አባቶች (ጳጳሳት) መምህራንንና መላው ሕዝበ ክርስቲያንን እንዲጠብቁና እንዲያስተዳድሩ በእግዚአብሔር መሾማቸውን የሚያስረዳ ምሥጢር አለው (ዮሐ.፳፩፥፩-፲፯)፡፡

ይህን የጌታችንን ትእዛዝና የሐዋርያትን ሥልጣነ ክህነት መሠረት በማድረግ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በዓመት ሁለት ጊዜ ጉባኤ ያደርጋል፤ የመጀመሪያው ጉባኤ ጥቅምት ፲፪ ቀን (የቅዱስ ማቴዎስ በዓል) ሲኾን፣ ሁለተኛው ደግሞ ርክበ ካህናት ነው፡፡ በዓሉ (ርክበ ካህናት) ወሩና የሚውልበት ቀን የበዓላትንና የአጽዋማትን ቀመር ተከትሎ ከፍና ዝቅ ቢልም በየዓመቱ የትንሣኤ በዓል በተከበረ በ፳፭ኛው ቀን በዕለተ ረቡዕ ይውላል፡፡ የአጽዋማትና የበዓላት ቀመር ከመዘጋጀቱ በፊት ማለትም በቅዱስ ድሜጥሮስ አማካኝነት ዐቢይ ጾም ሰኞ፣ ስቅለት ዓርብ፣ ትንሣኤ እሑድ፣ ርክበ ካህናት ረቡዕ፣ ዕርገት ሐሙስ፣ ጰራቅሊጦስ እሑድ እንዲኾን ከመደረጉ በፊት ርክበ ካህናት ግንቦት ፳፩ ቀን ይውል ነበር (መጽሐፈ ግጻዌ፣ ግንቦት ፳፩ ቀን)፡፡

ከዚህ በኋላ በዓለ ትንሣኤ በዋለ በ፳፭ኛው ቀን፣ በበዓለ ኃምሳ እኩሌታ በዕለተ ረቡዕ ርክበ ካህናት እንዲዘከር የቤተ ክርስቲያን አባቶች ወስነዋል፡፡ 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፣ማህበረ ቅዱሳን መካነ ድር

ዕርገት

‹ዕርገት› በግእዝ ቋንቋ ማረግ፣ ከታች ወደ ላይ መውጣት ማለት ሲኾን የጌታችን ትንሣኤ በተከበረ በዐርባኛው ቀን የሚውለው ዐቢይ በዓልም ‹ዕርገት› ይባላል (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፣ ገጽ ፯፻፷)፡፡ በዓለ ዕርገት ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ከተነሣ በኋላ ለዐርባ ቀናት በግልጽም በስውርም ለቅዱሳን ሐዋርያትና ለቅዱሳት አንስት መጽሐፈ ኪዳንን፣ ትርጓሜ መጻሕፍትን፣ ምሥጢራትን፣ ሕግጋትንና ቀኖናተ ቤተ ክርስቲያንን ሲያስተምር ቆይቶ ወደ ቀደመ ዙፋኑ ወደ ሰማይ በክብር በምስጋና ማረጉን በደስታ የምንዘክርበት ዐቢይ በዓል ነው፡፡ በዓለ ዕርገት በቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ በድምቀት ይከበራል፡፡ በዓሉ የሚውልበት ዕለት ሐሙስን ባይለቅም ቀኑ ግን የአጽዋማትና በዓላት ማውጫ ቀመርን ተከትሎ ከፍ እና ዝቅ ይላል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፣ማህበረ ቅዱሳን መካነ ድር

ጰራቅሊጦስ

በዓለ ጰራቅሊጦስ ወይም በዓለ ጰንጠቆስጤ ከዘጠኙ የጌታችን ዐበይት በአላት አንዱ ሲሆን መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት የወረደበትን ቀን የምናስብበት በዓል ነው። ሁሉ በሥርዓት ይሁን ብሎ ሐዋርያው እንዳስተማረን በቤተክርስቲያናችን የበዓላት ሥርዓት መሠረት ከትንሣኤ በኋላ ፶ኛው ቀን በዓለ ጰራቅሊጦስ/በዓለ ሃምሳ/በዓለ ጰንጠቆስጢ ወይንም የቤተክርስቲያን የልደት ቀን በመባል ይታወቃል ወይንም ይከበራል። ጰራቅሊጦስ የግሪክ ቃል የሆነ የመንፈስ ቅዱስ መጠሪያ ነው። ትርጉሙም በጐን የሚቆም፣ የሚረዳ፣ የሚያጽናና ማለት ነው። አበው መንጽሂ /የሚያነጻ፣ የሚቀድስ/ መጽንሂ /የሚያጸና፣ የሚያበረታ/ በማለት ይገልጹታል። ጰንጠቆስጤ የሚለውም የግሪክ ቃል ሲሆን “ፔንዲኮንዳ” ሃምሳ “ፔንዲኮስቲ” ሃምሳኛ ማለት ነው። በዓሉ ጌታችን ባረገ በአሥረኛው ቀን ከሙታን ተለይቶ በተነሳ በሃምሳኛው ቀን ይከበራል።

 

የበዓሉ የትመጣ

እስራኤል ከግብጽ ከወጡና ሕገ ኦሪት ከተሰጠቻቸው ጊዜ ጀምረው በዓለ ፋሲካን ለማክበር በኢየሩሳሌም ይሰበሰባሉ። ፋሲካ ለእስራኤል የነፃነት በዓላቸው ስለሆነ በስደት ምክንያት ወደ ተለያዩ ሀገሮች ከተበተኑ በኋላም እንኳን ካሉበት በመምጣት በዓሉን የሚያከብሩ ሲሆን ከፋሲካ ማግስት ጀምረው ሃምሳውን ቀን በዓል አድርገው አገር የቀረበው በየአገሩ እየሄደ አገር የራቀበት ስንቁን ይዞ ከዚያው ከኢየሩሳሌም ይሰነብታል። በሃምሳኛው ቀን በዘፀ ፴፬፥፳፪፣ በዘሌዋ ፳፫፥፲-፲፯ በታዘዙት መሠረት በዓለ ሰዊትን /የእሸት በዓልን/ ካመረቱት ምርት በኩራቱን ለመሥዋዕት በማቅረብ ያከብራሉ። በዓለ ፋሲካን ለማክበር ከዝርወት ተሰብስበው የነበሩ አይሁድ ሁሉ ወደየመጡበት የሚመለሱት ይህን በዓለ ሰዊትን ካከበሩ በኋላ ነው። በዓለ ሰዊትን በዝርወት የተሰበሰቡና በዚያውም የሚኖሩ አይሁድ አብዛኛውን ጊዜ በዓል የሚያከብሩት በደብረ ጽዮን ነው። 

በዚሁ ልማድና ሥርዓት መሠረት ጌታችን በመሥቀል ተሰቅሎ ድኅነተ ዓለምን በፈጸመበት ዓመት እስራኤላዊያን በዚች በደብረ ጽዮን በዓለ ሰዊትን ለማክበር ተሰብስበው እንዳሉ ሐዋርያት ደግሞ ጌታችን የነገራቸውን ተስፋ እየተጠባበቁ በዚሁ በደብረ ጽዮን በቅዱስ ማርቆስ እናት ቤት ውስጥ ተሰብስበው ነበር። ይህች ቀን ጌታ ባረገ አሥረኛው ቀን ነበረች። በዚህች ዕለት ጠዋት አይሁድ የቀድሞውን በዓል ሲያከብሩ ለሐዋርያት ጌታ የነገራቸው የተስፋ ቃል ተፈጸመላቸው፤ መንፈስ ቅዱስ ተሰጣቸው /ሐዋ ፪፥፩-፬/ በማለት በሐዋርያት ሥራ ላይ ጽፎልናል። ስለዚህም ቅዱሳን ሐዋርያት በዲድስቅሊያ 31 “ከዕርገቱ ቀን በኋላ ታላቅ በዓል ይደረግ፤ በዚህች ቀን በሦስተኛው ሰዓት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጰራቅሊጦስን ልኮልናልና እኛም በእርሱ ስጦታዎች ተሞላን አዳዲስ ቋንቋን ተናገርን” በማለት በዓሉን በቤተ ክርስቲያን እንድናከብር ሥርዓትን ሠርተዋል። በዚህም መሠረት በነቢያትና በሐዋርያት ትምህርት ላይ የታነጸችው ቤተ ክርስቲያናችንም ይህንኑ በዓል ዛሬም ድረስ ታከብራለች።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፣ማኅበረ ቅዱሳን አሜሪካ ማዕከል

ጾመ ሐዋርያት እና ጾመ ድኅነት

በዓለ ጰራቅሊጦስን ተከትለው ሁለት ዐበይት አጽዋማት ይጀመራሉ፡፡ እነዚህም ጾመ ሐዋርያት እና ጾመ ድኅነት (ረቡዕና ዓርብ) ሲኾኑ፣ ቍጥራቸውም ከሰባቱ አጽዋማት ነው፡፡

በቅዱሳት መጻሕፍት ተመዝግቦ እንደምናገኘው በብሉይ ኪዳን ነቢዩ ሙሴ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቀበለውን ሕገ ኦሪት ለሕዝቡ ከማስተማሩ በፊት ጾሟል (ዘፀ.፴፬፥፳፰)፡፡ ቅዱሳን ነቢያትም የተስፋውን ቃል መፈጸም እየተጠባበቁ እግዚአብሔርን ውረድ፤ ተወለድ እያሉ ይጾሙ፣ ይጸልዩ ነበር፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጾም የምግባር መሠረት መኾኑን ሊያስተምረን ወንጌልን ከመስበኩ አስቀድሞ ጾሟል (ማቴ.፬፥፩-፲፩)፤ ሐዋርያትም በበዓለ ኀምሳ መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላ ሕገ ወንጌልን ለሕዝቡ ከማስተማራቸው አስቀድሞ ጾመዋል፡፡ እኛም እነርሱን ተከትለን፣ በእነርሱ ሥርዓት በመመራት፣ በሐዋርያት ላይ ያደረው የመንፈስ ቅዱስ ጸጋና ሀብት በእኛም ላይ እንዲያድርብን በየዓመቱ ጾመ ሐዋርያትን እና ጾመ ድኅነትን፣ ሌሎችንም አጽዋማት አክብረን መጾም እንደሚገባን በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ተወስኗል (ፍት.ነገ. ፲፭፥፭፻፹፮)፡፡

ጾመ ሐዋርያት ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ተቀብለው በመላው ዓለም ተዘዋውረው ወንጌልን ከመስበካቸው በፊት የጾሙት ጾም ነው፡፡ ጾመ ድኅነት ደግሞ ስያሜው እንደሚያመለክተው ‹የመዳን ጾም› ማለት ሲኾን፣ ይህም በብሉይ ኪዳኑ አጽዋማት በጾመ አስቴር እና በጾመ ዮዲት የተተካ የሐዲስ ኪዳን ጾም ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን በሐማ ምክንያት በእስራኤል ላይ ታውጆ የነበረው ሞት በጾመ አስቴር እንደ ተሻረ ዅሉ፣ በሐዲስ ኪዳንም በዕለተ ረቡዕ በጌታችን ላይ በተፈጸመው ምክር የሰይጣን ሴራ ፈርሷልና በጾመ አስቴር ምትክ ረቡዕን እንጾማለን፡፡

በብሉይ ኪዳን በጾመ ዮዲት ምክንያት ሆሎሆርኒስ ድል እንደ ተደረገበት ዅሉ፣ በሐዲስ ኪዳንም መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ዓርብ በመስቀል ላይ በከፈለው መሥዋዕትነት ዲያብሎስ ድል ተደርጓልና በጾመ ዮዲት ምትክ ዓርብን እንጾማለን፡፡ ዕለተ ረቡዕ የጌታ ሞት የተመከረበት፤ ዓርብም አምላካችን የተሰቀለበት ዕለት ነውና በመስቀሉ መሥዋዕትነት ያገኘውን ድኅነት ዘወትር ማሰብ ስለሚገባን ዅልጊዜ እንድንጾማቸው በቅዱስ ሲኖዶስ ሥርዓት ተሠርቶልናል፡፡ የእነዚህ የሁለቱ ቀናት (የረቡዕ እና ዓርብ) ጾም ‹ጾመ ድኅነት› ይባላል፡፡

በአጠቃላይ ጾመ ሐዋርያትና ጾመ ድኅነት እንደ ጾመ ነነዌና ዐቢይ ጾም የበዓላትና የአጽዋማት ማውጫ ቀመርን ተከትለው የሚመጡ ከሰባቱ አጽዋማት መካከል የሚመደቡ የጾም ጊዜያት ናቸው፡፡ የጾመ ሐዋርያት ፋሲካ (መፈጸሚያ) የቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ በዓለ ዕረፍት (ሐምሌ ፭ ቀን) ሲኾን፣ ጾመ ድኅነት ግን ከበዓለ ኀምሳ በስተቀር ዓመቱን ሙሉ የሚጾም ጾም በመኾኑ ፋሲካው በዓለ ትንሣኤ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፣ማህበረ ቅዱሳን መካነ ድር

ጾመ ፍልሰታ

ጾመ ፍልሰታ ሐዋርያትን አብነት አድርገው ሐዋርያት የተቀበሉትን በረከት ለማግኘት ኦርቶዶክሳዊያን የሚጾሙት ጾም ነው። ፍልሰታ የግዕዝ ቃል ሆኖ ፈለሰ ከሚለው የግዕዝ ግስ የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም ተለየ፣ ሄደ፣ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ መሄድን ያመለክታል።

 

እመቤታችን እንደ ሰው ልማድ ሞትን ትቀምስ ዘንድ ግድ ስለሆነ ጻዕርና ሕማም በሌለበት አሟሟት በተወለደች በ64 ዓመቷ ጥር 21 ቀን 48 ዓ.ም. ከዚህ ዓለም በሞተ ሥጋ አርፋለች። ሐዋርያትም እንደምታርፍ በመንፈስ ቅዱስ ስለተገለጸላቸው ከያሉበት ወደ መኖሪያ ቤቷ (የዮሐንስ ቤት) መጥተው ነበር። ነፍሷ ከሥጋዋ እንደተለየች አስከሬኗን ገንዘውና ከፍነው ወስደው ለመቅበር ወደ ጌቴሴማኒ ሲሄዱ አይሁድ ሰምተው መጡና ሐዋርያትን ከበቧቸው። የአይሁድ ተንኮል አስከሬኗን ከሐዋርያት እጅ ቀምተው በእሳት ለማቃጠል ነበር፤ ይህንም ማድረግ የፈለጉት የሐዋርያት ትምህርት የጌታችን ከሞት መነሣትና ለፍርድ ተመልሶ መምጣት ከአይሁድ አልፎ ዓለም ሁሉ እያመነበት ስለመጣ እመቤታችንም ተነሥታ ዐርጋለች እያሉ ሐዋርያት ያስተምራሉ በሚል ስጋት ነበር። የፈሩት ይነግሣል የጠሉት ይወርሳል እንዲሉ የእመቤታችን ትንሣኤም ሆነ ዕርገት አይቀሬ ሆኗል።

አይሁድ የእመቤታችንን ሥጋ ለመንጠቅ በሞከሩበት ጊዜም ታውፊኒያ የተባለ ጎልማሳ ሰው በጉልበቱና በድፍረቱ በአይሁድ ዘንድ ተመርጦ ሥጋዋ ያረፈበትን ቃሬዛ ከሐዋርያት ነጥቆ መሬት ላይ ለመጣል ሲሞክር የእግዚአብሔር መልአክ በእሳት ሰይፍ ሁሉቱንም እጆቹን ቀንጥሶ ጥሏቸዋል። ነገር ግን ጥፋቱን አውቆ ወዲያው ስለተፀፀተና ይቅርታ ስለጠየቀ በአምላክ ፈቃድ በእመቤታችን አማላጅነት በቅዱስ ጴጥሮስ አማካኝነት እጆቹ እንደገና ተመልሰውለት የእመቤታችንን እመ አምላክነትና ክብር ለመመስከር በቅቷል።

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥጋ በመላእክት ተነጥቆ ከተወሰደ በኋላ በገነት ውስጥ በዕፀ ሕይወት ሥር ይቀመጥ እንጂ ከዮሐንስ በስተቀር ለሌሎች ሐዋርያት ለጊዜው ምሥጢር ሆኖባቸው ቆይቶ ነበር። ቆየት ብሎ ግን ዮሐንስ ስለሥጋዋ ነግሯቸዋል።

ሐዋርያትም ለእመቤታችን ካላቸው ክብርና ፍቅር የተነሳ ለምን አልቀበርናትም? ለምንስ የሥጋዋ ምሥጢር ይደበቅብናል? በማለት እያዘኑና እየለመኑ ለስድስት ወራት ከአሥር ቀናት ቆይተዋል። ከዚህ በኋላም ከነሐሴ 1 ቀን ጀምረው ሱባዔ ይዘው ለ14 ቀናት እግዚአብሔርን በጾምና በጸሎት ጠየቁት። በመጨረሻም የነገሩትን የማይረሳ የለመኑትን የማይነሳ ልጇ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነሐሴ 14 ቀን ሥጋዋን አምጥቶ ስለሰጣቸው ሳይውሉ ሳያድሩ በዕለቱ በጌቴሴማኒ በታላቅ ክብርና ዝማሬ ቀበሯት። በተቀበረችም በ3ኛው ቀን በነሐሴ 16 ከተቀበረችበት መቃብር ተነሥታ ወዲያውኑ በታላቅ ክብር በመላእክት አጃቢነት ወደ ሰማይ ዐርጋለች።

ጥበበኛው ሰሎሞንም “ውዴ  እንዲህ ይለኛል ሙሽራዬ ውዴ ሆይ! ተነሺ የእኔ ውብ ሆይ ነዪ አብረን እንሂድ” በማለት አመሣጥሮ የተናገረው በጥበበ እግዚአብሔር ተመርቶ እንደ ክርስቶስ ሆኖ ውዴ ያላት እመቤታችን መሆኗንና ልጇ ተነሥቶ እንደ ዐረገ እሷም መነሣቷንና ማረጓን እንረዳለን። /መሓ ፪፥፲/።

እመቤታችን ባረገችበት ጊዜ ቶማስ በመንፈስ ቅዱስ ጥበብ በደመና ተጭኖ ከሀገረ ስብከቱ /ሕንድ/ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመለስ እመቤታችን በመላእክት ታጅባ ወደ ሰማይ ስታርግ ተገናኙ። በዚህ ጊዜ ቶማስ ቀድሞ የልጇን ትንሣኤ ሳላይ አሁንም ደግሞ እርሷን ሳልቀብራት ከትንሣኤዋም ሳልደርስ ቀረሁ ብሎ አዘነ፤ ሆኖም እመቤታችን ዕርገቷን ከእርሱ በስተቀር ሌሎች አለማየታቸውን ገልጻ አረጋጋችው፤ ዕርገቷንም ለሐዋርያት እንዲነግርና ምልክትና ማስረጃ እንዲሆነው ተገንዛበት የነበረውን ሰበኗን /የከፈን  ጨርቅ/ ሰጥታ አሰናበተችው።

ቶማስም መሬት ለይ ወርዶ መቀበሯን፣ ትንሣኤዋንና ዕርገቷን ያላወቀ መስሎ ሐዋርያትን ስለ እመቤታችን ሥጋ ጉዳይ ጠየቃቸው፤ እነርሱም ሱባዔ ገብተው እግዚአብሔርን በጸሎት መጠየቃቸውን፣ ከሱባዔያቸው በኋላ የእግዚአብሔር ፈቃዱ ሆኖ ሥጋዋን መላእክት አምጥተው እንደሰጧቸውና እንደቀበሯት አስረዱት። እርሱ ግን ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር እንዴት ሊሆን ይችላል? ሲል ተከራከራቸው። ሐዋርያትም ቶማስን ለማሳመን መቃብሯን ለማሳየት ወሰዱት ሆኖም መቃብሯ ባዶ ሆኖ አገኙትና ተደናገጡ፤ በዚህ ጊዜ ቶማስ የሆነውን ሁሉ ገልጾ ለምልክትና ለማረጋገጫ የሰጠችውን ሰበኗን /ተገንዛበት የነበረውን ጨርቅ/ የራሱን ድርሻ አስቀርቶ አከፋፍሎ ሰጣቸው ዛሬም ካህናቱ ከእጅ መስቀላቸው ጋር መሐረብ የሚይዙበት ምክንያት ሐዋርያት የተከፋፈሉት የእመቤታችን ሰበን ምሳሌ ነው።

ሐዋርያትም የዕርገቷን ምሥጢር ካመኑ በኋላ ዕርገቷን ለማየት በዓመቱ በተመሳሳይ ሁኔታ እንደገና ከነሐሴ 1 ቀን ጀምረው ለሁለተኛ ጊዜ ለሁለት ሱባዔ ገቡ፣ እግዚአብሔርም ልመናቸውን ሰምቶ በነሐሴ ወር በ16ኛው ቀን ጌታችን ሐዋርያትን ወደ ሰማይ አውጥቷቸው እመቤታችንን አግኝተዋት ከሷ ተባርከው በታላቅ ደስታ ወደ ደብረዘይት ተመልሰዋል።

በአጠቃላይ የእመቤታችን ለሐዋርያት በተለያዩ ጊዜያት መታየት፣ የሥጋዋና የነፍሷ ከቦታ ቦታ መንቀሳቀስ ፍልሰት ሲባል ከዚህ የተነሣ የነሐሴ ጾም በቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት መሠረት ሐዋርያት ያገኙትን በረከት ለማግኘት ጾመ ፍልሰታን እንጾማለን።

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፣ማኅበረ ቅዱሳን አሜሪካ ማዕከል

የአብርሃሙ ሥላሴ

ሐምሌ ፯ ቀን እግዚአብሔር በአብርሃም ቤት ተገኝቶ የይስሐቅን መወለድና የእግዚአብሔርን ሰው መኾን ከመናገሩ በተጨማሪ የአብርሃምን ዘሩን እንደሚያበዛለትና አሕዛብ ኹሉ በእርሱ እንደሚከብሩ ማለትም ከአብርሃም ዘር በተገኘው በኢየሱስ ክርስቶስ አሕዛብ እንደሚቀደሱና ይህንን ምሥጢርም እግዚአብሔር ከወዳጁ ከአብርሃም እንደማይሠውር ቃል የገባለት ቀን ነው፡ በተጨማሪም እግዚአብሔር በኀጢአታቸው የተነሣ ሰዶምንና ገሞራን ያጠፋው አብርሃምም በአማላጅነት በፊቱ የቆመው በዛሬው ዕለት ነው፡፡


ከዚህ የእግዚአብሔር በአብርሃም ቤት መገለጥ ታሪክ እግዚአብሔር እንደ አብርሃም ልቡናቸው ቅን በኾነና በለጋሾች ማለትም ምጽዋትንና እንግዳ መቀበልን የዘወትር ልማዳቸው አድርገው በሚኖሩ ሰዎች ቤት እንደሚገኝ፤ እግዚአብሔር በረድኤቱ ወደ ሰው ቤት ሲገባም የተዘጋ ማሕፀን እንደሚከፍትና ቤቱን በበረከት እንደሚሞላ፤ እንደዚሁም የተሠወረ ምሥጢር እንደሚገልጽ እንረዳለን፡፡ ለዚህም እግዚአብሔር በአብርሃም ቤት ገብቶ ያደረገው ኹሉ ትልቅ ማስረጃ ነው፡፡ ከዚሁ ኹሉ ጋርም እግዚአብሔር አምላክ በአንድነቱም በሦስትነቱም እየታየ አምላክነቱን እንደሚገልጥና የቸርነቱን ሥራ እንደሚሠራም ከዚህ ታሪክ እንማራለን፡፡


ይህ የእግዚአብሔር በአብርሃም ቤት መገለጥ በአንድ ወቅት ብቻ የተፈጸመና *ነበር* እየተባለ የሚነገር ታሪክ ሳይኾን፣ ለዘለዓለሙ ሲነገርና ሲፈጸም የሚኖር ሕያው ትምህርት ነው፡፡ ይህንንም እግዚአብሔር ለቅዱሳኑ በልዩ ልዩ መንገድ እየተገለጠ ለዘመናት በሚያደርገው ድንቅ ሥራና ተአምር መገንዘብ እንችላለን፡፡

ዛሬም ሀብት ንብረት ያለን ምእመናን በትሩፋት ሥራ በመሠማራት ማለትም እንግዶችን በመቀበል፣ ለተራቡ በማብላት፣ በመመጽወት ተግባር ከኖርን፤ በቂ ንብረት የሌለን ደግሞ ልቡናችንን ንጹሕ ከማድረግና ከኀጢአት ከመራቅ በተጨማሪ ቤት ላጡና ለተቸገሩ መራራትን፣ ደግነትን፣ ቀና አስተሳሰብን ገንዘብ ካደረግን እግዚአብሔር በሕይወታችን ውስጥ አድሮ ይባርከናል፤ ይቀድሰናል፡፡ በአጠቃላይ የምንሻውን መልካም ነገር ኹሉ ይፈጽምልናል፡፡

ምንጭ፣ማህበረ ቅዱሳን መካነ ድር

ደብረ ታቦር

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ካሏት መንፈሳዊ በዓላት አንዱ የደብረ ታቦር በዓል ነው። ይህ በዓል ከጌታችንና ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ዘጠኙ ዐበይት በዓላት አንዱ ነው። ደብረ ታቦር ወይም የታቦር ተራራ ጌታ በምድረ እስራኤል እየተዘዋወረ በማስተማር ላይ በነበረ ዘመን ነሐሴ 13 ቀን ብርሃነ መለኮቱንና ክብረ መንግሥቱን የገለጠበት ነው።

 

ጌታችን በቂሳርያ ሐዋርያትን “ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ብለው ይጠሩታል?” በማለት ከጠየቃቸው ከስድስት ቀናት በኋላ ዘጠኙን ሐዋርያት ከእግረ ደብር ትቶ ሦስቱን ማለትም ጴጥሮስን፣ ዮሐንስንና ያዕቆብን አስከትሎ ከርዕሰ ደብር ወጣ። በተራራው ላይ ሳሉ የጌታችን መልክ ተለወጠ። ፊቱ እንደ ፀሐይ አበራ፤ ልብሱም እንደ በረዶ የነጻ ሆነ። በዚህ ጊዜ ብርሃነ መለኮቱን ክብረ መንግሥቱን ገለጸ። ሙሴና ኤልያስም ከእርሱ ጋር ሲነጋገሩ ተሰሙ። ሙሴና ኤልያስን መምረጡ ስለምንድር ነው ቢሉ ሙሴ 570 ጊዜ ቃል በቃል ተነጋግሮ ባይህ እወዳለሁ ባለው ጊዜ ፊቴን አይቶ አንድ ሰዓት እንኳ መቆም፣ መቆየት የሚቻለው የለም ቢለው ይህ ከሆነማ ባለሟል መባሌ ምኑ ላይ ነው ሲለው መሥዋዕት ሆኜ በምቀርብበት ጊዜ እታይሃለሁ ብሎት ነበርና /ዘጸ ፴፫፥፲፰-፳፫/ ያንን ለመፈጸም፤ ኤልያስም እንዲሁ ተስፋ ነበረውና። 

በዚህ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው። ብትፈቅድስ ሦስት ዳስ እንሥራ አንዱን ለአንተ፣ አንዱን ለሙሴ፣ አንዱን ለኤልያስ በማለት ተናገረ። ሙሴ ጠላት ይገድላል፣ ባሕር ይከፍላል፣ መና ያወርዳል፣ ውሃ ያፈልቃል፤ ኤልያስ ሰማይ ይዘጋል፣ ዝናብ ያቆማል፤ ክርስቶስ ቅዱሳኑ በጸጋ የሠሩትን ሥራ በባሕርይው ይፈጽማል፤ እነሱ ካሉ ሁሉም አለ ብሎ። ይህን ሲናገር ብሩህ ደመና መጥቶ ጋረዳቸው። ወዲያውም “ዝንቱ ውእቱ ወልድየ ዘአፈቅር ወሎቱ ስምዕዎ” /በእርሱ ደስ የሚለኝ ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት/ የሚል ድምጽ ተሰማ። እነጴጥሮስ ደንግጠው ወደቁ። ጌታ ኢየሱስም ቀርቦ ዳሰሳቸው። “ተነሱ አትፍሩ” አላቸው ዓይናቸውንም ገለጡ። ከተራራም ሲወርዱ ጌታ ኢየሱስ የሰው ልጅ ከሙታን ተለይቶ እስኪነሣ ድረስ ያያችሁትን ለማንም አትንገሩ ብሎ አዘዛቸው። 

ዘጠኙን በእግረ ደብር ትቶ ሦስቱን አስከትሎ መውጣቱ ስለምንድር ነው ቢሉ ከዘጠኙ ብርሃነ መለኮቱን ክብረ መንግሥቱን ሊያይ የማይገባው ይሁዳ ነበርና ብቻውን ቢተወው ከብርሃነ መለኮቱ ቢለየኝ በሞቱ ገባሁበት ይል ነበርና። ያስ ቢሆን ከተራሮች ሁሉ ታቦርን ስለምን መረጠ ቢሉ ዳዊት “ታቦር ወአርሞንኤም በስመ ዚአከ ይትፌስሑ” /ታቦርና አርሞንኤም በስምህ አምነው በተደረገላቸው ነገር ደስ ይላቸዋል/ ብሎ ነበርና ያን ለመፈጸም ነው።

ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃነ መለኮቱን ክብረ መንግሥቱን በገለጸበት በታቦር ተራራ አካባቢ በጐቻቸውን አሰማርተው ይጠባበቁ የነበሩ እረኞች አካባቢው በብርሃን ስለተሞላ ገና ያልመሸ መስሏቸው በዚያው ቆዩ። ልጆቻቸው ወደየቤታቸው በጊዜ ባለመመለሳቸው ግራ የተጋቡት ወላጆቻቸው ዳቦ በመያዝና ችቦ በማብራት ወደተሰማሩበት ሥፍራ ሲሄዱ በደህና አገኟቸው። በዚህ ታሪክ መሠረት በሀገራችን ወጣቶች ቡሄ (ደብረ ታቦር) ከመድረሱ በፊት ጅራፍ እየገመዱ ያጮሃሉ። እናቶችም ለበዓሉ የሚሆን ሙልሙል ለመጋገር ስንዴ ሲያጥቡ፣ ሲፈትጉና ሲያስፈጩ ይሰነብታሉ። በዓሉ እንደነገ ሊሆን እንደዛሬ በዋዜማው ነሐሴ 12 ቀን የየሰፈሩ ወጣቶች በየቤቱ እየዞሩ ቡሄ በሉ ሆ እያሉ ይጨፍራሉ። በዚህ ጊዜ እናቶች ካዘጋጁት ሙልሙል ዳቦ እያነሱ ይሰጧቸዋል። በነጋታው ነሐሴ 13 ቀን ማታ የመንደሩ ሰው አንድ ላይ በመሆን ችቦ ያበራል።

በደብረ ታቦር በዓል ሰሞን የጅራፉ ጩኸት ድምፀ መለኮትን፣ ጩኸቱ ማስደንገጡ ደግሞ ሦስቱ ሐዋርያት በድምፀ መለኮት ደንግጠው መውደቃቸውን ያስተምረናል። የቡሄ ዕለት ማታ ችቦ መብራቱ ደግሞ በደብረ ታቦር ለታየው ብርሃነ መለኮትና ወላጆች ልጆቻቸውን ለመፈለግ ላበሩት ችቦ ምሳሌ ነው። በበዓሉ ዕለት የቅርብ እውቂያ ላለው እያንዳንዱ ቤተሰብ ልጆች ልክ ዳቦ ይሰጣል። ይህም በዕለቱ ወላጆች ለልጆቻቸው ዳቦ ይዘው ለመሄዳቸው ምሳሌ ነው።

በሀገራችን በሚገኙ መንፈሳዊ ትምህርት ቤቶች ውስጥ ደግሞ ደብረ ታቦር የተማሪዎች በዓል ነው። ተማሪዎች ቀደም ብለው “ስለደብረ ታቦር” እያሉ እህል፣ ጌሾና ብቅል ይለምናሉ። ሕዝቡም ባሕሉን ስለሚያውቀው በገፍ ይሰጣቸዋል። እነርሱም ጠላ ጠምቀው፣ ቆሎ ቆልተውና ዳቦ ጋግረው የደብረ ታቦር ዕለት ሊያስቀድሱ ወደ ቤተ ክርስቲያን ለሚመጡ ምዕመናን ከቅዳሴ በኋላ ይጋብዛሉ። ይህ እስካሁን በመንፈሳዊ ትምህርት ቤቶች የሚሠራበት ነባር ባሕላችን ነው።

ስለዚህ ይህንን ታላቅ ሃይማኖታዊ በዓልና ነባር ባሕል በመጠበቅ ለትውልድ ማስተላለፉ ተገቢ ነው። በተለይ በአሁኑ ወቅት ቤተ ክርስቲያንን ታሪክ አልባ ለማድረግ በየአቅጣጫው ለተነሱ ምንደኞች እውነተኛውን የቤተ ክርስቲያን ታሪክና ባሕል በማስረዳት ክብሯ ተጠብቆ እንዲኖር መጣር ከሁላችንም ይጠበቃል። በደብረ ታቦር የታየው ድንቅና የማይረሳ ታሪክ ተጠብቆ ለትውልድ መተላለፍ አለበት። በተለይ በአሁኑ ጊዜ የቡሄ በሉ ጭፈራ ሳይቀር ታዋቂ ስፖርተኞችን፣ ዘፋኞችንና አርቲስቶችን ማወደሻ እየሆነ ስለመጣ “አንድ ሞኝ የተከለውን አምሳ ሊቃውንት አይነቅሉትም” እንደተባለ ሳይቃጠል በቅጠል እንዲሉ ሁሉም ኦርቶዶክሳዊ ለቤተ ክርስቲያኑ መቆም አለበት። ቤተ ክርስቲያናችንን መጠበቅ፣ ማሳደግና ለዓለም ማስተዋወቅ የሁላችንም ኃላፊነት ነው።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፣ማኅበረ ቅዱሳን አሜሪካ ማዕከል

Please reload

ዘመን መለወጫ
Mesqel
tsige
Nebiyat
Lidet
gehad
Timqet
nenewe
Abiy
Debrezeyit
Hossana
Himamat
Seqlet
Tinsae
erget
Peraqlitos
Tsome Hawariyat
Tsome filseta
Estifanos
rikbe kahinat
Tir silase
hamle silase
Debre tabor
bottom of page